የአማራ ጸረ ሙስና ኮሚሽን በሙስና ተከሰሰ

የካቲት ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በአማራ ክልል የሚሰሩ የተለያዩ የመንግስት መስሪያቤት ሰራተኞች እና የኢህአዴግ አባላት ለኢሳት እንደገለጡት ከመሬት ሽያጭ ጋር በተያያዘ በክልሉ የሚታየው ከፍተኛ ሙስና ሊገታ ያልቻለው የክልሉ ጸረ ሙስና ኮሚሽን በሙስናው ዋና ተዋናይ ሆኖ በመገኘቱ ነው።

ሰራተኞቹ ከወራት በፊት ከፍተኛ የዜና ሽፋን ተሰጥቶት የነበረውን የሙስና ጉዳይ በማንሳት እንደገለጡት ፣ የክልሉ ባለስልጣናት ከባለሀብቶች ጋር በመመሳጠር በባህርዳር ከተማ ከፍተኛ የሆነ የመሬት ችብቸባ እያካሄዱ ቢሆንም፣ የክልሉ የጸረ ሙስና  ኮሚሽን በሙስና ተወናይ በመሆኑ አደጋውን ለመከላከል አልተቻለም።

በመሬት ላይ የሚካሄደውን ዘረፋ የሚመሩት የከተማው የኢንዱስትሪ ልማትና ከተማ አገልግሎት ጽ/ቤት ሰራተኞች የሆኑት አቶ ገብሩ ጸሀይነህ፣ አበ ሰማ፣   አየነው አለሙና በጊዜው ጸሀየ መሆናቸውን ሰራተኞች ይገልጣሉ።

የክልሉ የጸረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ የሆኑት መቶ አለቃ እንዳለው አራቱ ግለሰቦች የከተማውን መሬት በድርድር በመሸጥ  የሚጠረጠሩ መሆናቸውን በመግለጽ በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንዲውሉ ካስደረጉ በሁዋላ፣ አርብ ጥቅምት 30/2005 ዓም ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ተደርጓል።

አራቱ ተከሳሾች ፍርድ ቤት ሲቀርቡ በከተማዋ የሚገኙ ባለሀብቶች ፍርድ ቤቱን ያጨናነቁ ሲሆን፣ ዳኛውም የተከሳሾችን ፋይል አይተው ዋስትና ያሰጣል አያሰጥም በማለት ለመወሰን የጊዜ ቀጠሮ ሰጥተው ፋይሉን ወደ መዝገብ ቤት ከመሩት በሁዋላ፣ የጸረ ሙስና ኮሚሽነሩ ተከሳሾች የዋስትና መብት ይፈቀድላቸው የሚል ደብዳቤ ዳኞች እንደገና ችሎት እንዲሰየሙ ተደርጎ እያንዳንዳቸው በ5 ሺ ብር ዋስ እንዲለቀቁ ተደርጓል።

በስፍራው የነበሩ አንድ ባለሀብት ለሁሉም ተከሳሾች የዋስትና ገንዘብ በማስያዝ እንዲለቀቁ አድርገዋል።

ሰራተኞቹ እንደገለጡት የጸረ ሙስና ኮሚሽን ባለስልጣናት እስረኞችን በዋስ ለማስለቀቅ 30 ሺ ብር፣ ክሱን ለመሰረዝ ደግሞ 150 ሺ ብር ለመቀበል ከባለሀብቶች ጋር ተደራድረዋል። በከፍተኛ ሙስና የተከሰሱት ሰራተኞች ላለፉት ሶስት ወራት አንድም ቀን ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ቀድሞ በነበራቸው የሀላፊነት ቦታዎች ላይ እየሰሩ እንደሚገኙ  ታውቋል። አብዛኛውን ውሎውን በመስሪያ ቤቱ አድርጎ የነበረው የኮሚሽኑ ባለስልጣንም ምርመራውን ማቋረጡ ታውቋል።

ተጠርጣሪ ግለሰቦቹ ቀደም ሲል ኢሳት ይፋ ያወጣው የሙስና ወንጀል መሪ ተወናይ ከሆኑት ከባህርዳር ከተማ አቶ ስማቸው ወንድማገኝ ጋር ጥብቅ የጥቅም ቁርኝት እንዳላቸው ታውቋል።

የባህርዳር ጸረሙስና ኮሚሽን መስሪያቤትን ለማነጋገር ያደረግነው ጥረት አልተሳካም።