የአለም ባንክ እና ኢትዮጵያ ውዝግብ ውስጥ ገቡ

ግንቦት ፳ (ሀያ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ላለፉት 20 አመታት ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ከሞላ ጎደል ጥሩ የሚባል ግንኙነት የነበረው የአለም ባንክ በሀይል ከሚፈናቀሉ ዜጎች ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ውዝግብ ውስጥ መግባቱ ታውቋል።

ሂውማን ራይትስን ጨምሮ ሌሎች አለማቀፍ የሰብአዊ መብቶች ተከራካሪ ድርጅቶች የኢትዮጵያ መንግስት በጦር ሀይል በመታገዝ ከ45 ሺ በላይ የጋምቤላ ተወላጆችን በግዴታ ማስፈሩን ተቃውመው ነበር።

የአለም ባንክ አንድ ገለልተኛ ቡድን በማቋቋም ክሱን ለማጣራት ባለፈው ጥቅምት ወር እንቅስቃሴ የጀመረ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ መንግስትም ከአጣሪ ቡድኑ ጋር እንደማይተባበር ይፋ አድርጓል።

የጠቅላይ ሚ/ር ሀይለማርያም ደሳለኝ ቃል አቀባይ የሆኑት አቶ ጌታቸው አረዳ ከአጣሪ ቡድኑ ጋር እንደማይተባበሩ ዘገባውን ላወጣው ብሉምበርግ ገልጸዋል። “ከአለም ባንክ ጋር እንተባበራለን ነገር ግን አለም ባንክ ካቋቋመው አጣሪ ኮሚቴ ጋር አንተባበርም” ብለዋል ቃል አቀባዩ።

የአለም ባንክ አጣሪ ቡድን በመጀመሪያ ሪፖርቱ ባንኩ የሚሰጠው ገንዘብ ዜጎችን በሀይል ከማፈናቀል ጋር የሚያያዝ መሆኑን ማመልከቱ የኢትዮጵያን መንግስት ሳያስቆጣ አልቀረም።

የኢትዮጵያ መንግስት አጣሪ ቡድኑ በኢትዮጵያ ላይ  የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ከጀመሩት ከእነ ሂውማን ራይትስ ጋር ግንኙነት አለው ይላል።

አንድ የሰብአዊ መብት ድርጅት ተከራካሪ የአለም ባንክ አባል የሆነ አገር ባንኩ ካቋቋመው አካል ጋር አልተባበርም ማለቱ ያልተጠበ ነው በማለት ለብሉምበርግ ገልጸዋል።

የአለም ባንክ ” አትጠይቁኝ” የሚለውን የኢትዮጵያን  መንግስት ከዚህ በሁዋላ ሲረዳ አይታየኝም በማለት ባለስልጣኑ አክለዋል።

አትዮጵያ አምና ብቻ 3 ቢሊዮን 5 መቶ ሚሊዮን ዶላር ወይም ከ60 ቢሊዮን ብር  ያላነሰ ገንዘብ በእርዳታ አግኝታለች።