የንዌር ዞን ግጭት ተባብሶ ቀጠለ

ጥቅምት ፰(ስምንት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም

ኢሳት ዜና :-ሰሞኑን በጋምቤላ ክልል ንዌር ዞን ዋና ከተማ በሆነችው ሚኒኛንግ ከተማ የተፈጠረው ግጭት ተባብሶ የሞቱ የመከላከያ ሰራዊት ቁጥር መጨመሩና በርካታ መሳሪያዎች ከመከላከያ ካምፕ መወሰዳቸው ተገለጸ፡፡

ባለፋው እሁድ አንድ መሳሪያ የታጠቀ ሰው እግር ኳሱን ሲመለከቱ በነበሩ ሰዎች መካከል ባስነሳው አለመግባባት የመከላከያ ሰራዊት አባላት እና ነዋሪዎች ግጭት ውስጥ ገብተው ሰንብተዋል፡፡

ግጭቱ ተባብሶ በመቀጠሉ ሰሞኑን ከሞቱት ሶስት የሰራዊት አባላት በተጨማሪ አራት መሞታቸውን ተባባሪያችን እና የአኝዋክ ሬዲዮ አዘጋጅ የሆነው ጋዜጠኛ አኑአ ጊሎ ተናግሯል፡፡

ከነዚህም በተጨማሪ የሞቱ የአካባቢው ነዋሪዎች ቁጥር ስድስት መድረሱንና ውጥረቱ ተባብሶ መቀጠሉን ለማወቅ ተችሏል፡፡

የመከላከያ ሰራዊት በወሰደው እርምጃ የተቆጡ የዞኑ ሚሊሺያዎች ከህዝብ ጎን በመቆም ተቃውሟቸውን እየገለጹ እንደሚገኝ አኑአ ጊሎ ገልጿል፡፡

በዞኑ የሚገኙ የመከላከያ የሰራዊት ካምፕ ላይ በደረሰ ዘረፋም በርካታ መሳሪያዎች መወሰዳቸውን የተናገረው ጋዜጠኛው የዞኑ የመንግስት አካላትና የመከላከያ ሰራዊት ተወካዮች መሳሪያዎች በሚመለሱበት ዙሪያ ምክክር ማድረግ ላይ እንደሆኑ አመልክቷል፡፡

ባለፈው እሁድ ግጭቱን ተከትሎ የንዌር ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አፈ ጉባኤ መሞታቸውን መዘገባችን የሚታወስ ነው፡፡

ግጭቱ በማይረባ አለመግባባት ይከሰት እንጂ የባለስልጣናቱ ግድያ ሌላ አጀንዳ ሊኖረው እንደሚችል የአካባቢው ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡