የቁጫ ወረዳ የአገር ሽማግሌዎች “ለ16ኛ ጊዜ ጠ/ሚንስቴር ጽ/ቤት አቤት ብንልም የሚሰማን አጣን” አሉ

የካቲት ፳፰ (ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በደቡብ ክልል በጋሞ ዞን በቁጫ ወረዳ ከማንነትና ከመልካም አስተዳደር ጋር ተያይዞ የተነሳውን ተቃውሞ ተከትሎ በአካባቢው ያለው አፈና እንዲቀንስ ፣ በእስር ላይ የሚገኙ ሰዎች እንዲፈቱ እንዲሁም ከቀያቸውና ከስራቸው የተፈናቀሉት ዜጎች ወደ ቦታቸውና ወደ ስራቸው እንዲመለሱ ለመጠየቅ ትናንት ወደ አዲስ አበባ በማምራት ለጠ/ሚኒስቴር ጽ/ቤትና በፌደሬሽን ምክር ቤት ለ16ኛ ጊዜ አቤቴታቸውን ያቀረቡ የአገር ሽማግሌዎች መፍትሄ በማጣት ተመልሰዋል።

የህዝቡን ጥያቄ በመያዝ ወደ ጠ/ሚ ፅ/ቤት ከሄዱት የአገር ሽማግሌዎች መካከል አንዱ ለኢሳት እንደገለጹት፣ መንግስት የህዝብ ተወካይ የሆኑ የአገር ሽማግሌዎችንና ሌሎች ነዋሪዎችን ይዞ በማሰር ጥያቄ እንዳይመለስ ማድረጉን ገልጸዋል።

በወረዳው የተነሳውን የህዝብ ተቃውሞ ተከትሎ ከ240 በላይ ሰዎች በአርባ ምንጭ እስር ቤት ታስረው ሲገኙ፣ በመቶዎች የሚቆጠሩት ደግሞ ከስራ ተባረዋል።

በጉዳዩ ዙሪያ የክልል ባለስልጣናትን ለማነጋገር በተደጋጋሚ ሙከራ ብናደርግም አልተሳካልም።