በሚሊዮን ብር የሚቆጠር የህክምና መገልገያ መሳሪያዎችን ዘርፈዋል የተባሉ ተከሰሱ

ማጋቢት ፩ (አንድ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ሪፖርተር እንደዘገበው ከኢትዮጵያ መድኃኒት ፈንድና አቅርቦት ኤጀንሲ ግምታቸው ከ3.3 ሚሊዮን ብር በላይ የሆኑ የሕክምና መገልገያ መሣሪያዎችን በመስረቅ ወንጀል የተጠረጠሩ አዲስ በላይ እና ተባባሪዎቹ ሁሴን ከድር ፣ ማኒና ተስፋ ማርያም እና ታደሰ ባቲ ክስ ተመስርቶባቸዋል።

ሰባት ዓይነት የሕክምና መገልገያ መሣሪያዎችን የሰሌዳ ቁጥሩ አ.አ 3-37987 በሆነ አይሱዙ መኪና ጭነው ሊሰወሩ ሲሉ እንደተደረሰባቸው የፌዴራል የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ሕግ የካቲት 25 ቀን 2006 ዓ.ም. ጽፎ፣ የካቲት 26 ቀን 2006 ዓ.ም. ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አንደኛ ወንጀል ችሎት ያቀረበውን የክስ ቻርጅ በመጥቀስ ጋዜጣው ዘግቧል።

አዲስ በላይ የተባለው ተጠርጣሪ ተከሳሽ የኤጀንሲው ሠራተኛ ሲሆን፣ ሁሴን ከድር ማኒና ተስፋ ማርያም ታደሰ ባቲ የተባሉት ግለሰቦች ደግሞ የስርቆቱ ተባባሪዎች ተብለው በክሱ ስማቸው ሰፍሯል፡፡