የቀድሞዋ የህወሀት ታጋይ ወ/ሮ አዜብ መስፍንን ተቹ

ሚያዚያ ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ወ/ሮ አዜብ መስፍን የባለቤታቸው ወርሃዊ ደመወዝ አነስተኛ እንደነበር በመጥቀስ በኢህአዴግ ጉባዔ ላይ ያደረጉትን
ስሜታዊ ንግግር የሕዝብን የማመዛዘን ችሎታ ግምት ውስጥ ያላስገባ ነበር ሲሉ የቀድሞ የህወሃት ታጋይ ወ/ት
አረጋሽ አዳነ ተቹ፡፡
ወ/ት አረጋሽ በዛሬው ዕለት በአዲስአበባ ለንባብ በበቃው “ኢትዮ ምህዳር” ጋዜጣ በሰጡት ሰፊ ቃለምልልስ ላይ
የወ/ሮ አዜብን ንግግር አስመልክቶ ጠንከር ያለ ትችት ሰንዝረዋል፡፡አቶ መለስ በፔሮል 6ሺ500 ብር ደመወዝ
የሚከፈላቸው ብቸኛው መሪ እንደነበሩ ወ/ሮ አዜብ መናገራቸውን በመጥቀስ ጋዜጣው ላቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ
“የኢትዮጽያን ሕዝብ መቼም የማመዛዘን ችሎታ ያለው ነው፡፡የማስተዋል ችሎታ አለው፡፡ያውቃል፡፡የወ/ሮ አዜብ
አባባል ግን የሕዝብን የማመዛዘን ችሎታ በትክክል የሚመዝን አድርጌ አልወሰድኩትም፡፡ምክንያቱም ሕዝቡ እውነታው
ይህ እንዳልነበር ያውቃልና” ብለዋል፡፡
አያይዘውም ጠ/ሚ/መለስ ቤተመንግስት ውስጥ ነው የሚኖሩት፡፡ቤተመንግስት ደግሞ የራሱ አስተዳደር ያለው ትልቅ
ተቋም ነው፡፡ራሱን የቻለ ባጀት አለው፡፡ይህ ባጀት የት እንደሚውል የማይታወቅ አይደለም፡፡ቤተመንግስት ውስጥ
የሚኖሩ ሰዎች የሚተዳደሩበት፣የሚኖሩበት ነው፡፡እንግዶች የሚያስተናግዱበትና የሚጠሩበት በጀት አላቸው፡፡ይህ አሁን
የተፈጠረ ሳይሆን በፊትም የሚታወቅ ነገር ነው፡፡በየስብሰባው በሚሄዱበት ጊዜ ውጪ አገር ከሆነ በውጪ ምንዛሪ
ይከፈላቸዋል፡፡የአገር መሪ ስለሆነ የአልጋና የምግብ ሊከፍሉ አይችሉም፡፡ስለዚህ ምን ያህል የውጪ ገንዘብ
መሰብሰብ እንደሚቻል መገመት ይቻላል” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
እነአቶ መለስ ልጆቻቸውን ውድ የተባለ ት/ቤት እንደሚያስተምሩ ያስታወሱት ወ/ት አረጋሽ አዳነ ከዛሬ 12 እና
13 ኣመት በፊት ለአንዱ ልጃቸው ብቻ በዓመት 35 ሺ ብር ይከፍሉ እንደነበር አውቃለሁ ብለዋል፡፡ሶስቱም
ልጆቻቸው በዚህ ሁኔታ እንደተማሩ ቢታሰብ ገንዘቡ በዓመት 100ሺ ብር ይከፍሉ ነበር ማለት ነው ካሉ በኃላ ይህን
በስድስት ሺ ብር ደመወዝ ሊያደርጉት አይችሉም ብለዋል፡፡
በተጨማሪም ኢንዶውመንት የሚባለው ግዙፉ የኤፈርት ሐብት በወ/ሮ አዜብ ቁጥጥር ስር መሆኑም ወ/ት አረጋሽ
በማስታወስ በ6 ሺ ብር ገቢ ብቻ ኖረዋል የተባለውን አጣጥለውታል፡፡