የሼህ መሀመድ አላሙዲን ቤተሰቦች ታሰሩ

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 23/2010)

የሼህ መሀመድ አላሙዲን ቤተሰቦች ሳውዳረቢያ ውስጥ ታሰሩ።

የቢሊየነሩ ተውልደ ኢትዮጵያዊ ቤተሰቦች የታሰሩት ሼህ መሀመድ አላሙዲን በድርድር ገንዘብ ከፍለው ከእስር እንዲወጡ የቀረበላቸውን አማራጭ ባለመቀበላቸው እንደሆነም ተመልክቷል።

የሳውዳረቢያ መንግስት በቁጥጥር ስር ካዋላቸው ባለሃብቶች አንዱ የሆኑት ትውልደ ኢትዮጵያዊው ሼህ መሀመድ አላሙዲን በህዳር ወር ሳውዳረቢያ ሪያድ ውስጥ መታሰራቸው ይታወሳል።

በእሳቸው የተጀመረው እስር ደግሞ በቤተሰቦቻቸውም ላይ መቀጠሉን ነው ሚድል ኢስት ሞኒተር ትላንት ባወጣው ዘገባው ያሰፈረው።

በቤተሰቦቻቸው ላይ እስሩ የተከተለው ሌሎቹ ባለሃብቶችና ልኡላን በድርድር ገንዘብ ከልፈው ሲለቀቁ ሼህ መሀመድ አላሙዲን ገንዘብ ለመክፈልም ሆነ ንብረታቸውን አሳልፈው ለመስጠት ፈቃደኛ ባለመሆናቸው እንደሆነም ተመልክቷል።

በሳውዲው አልጋ ወራሽ መሀመድ ቢን ሰልማን በተመራው የጸረ ሙስና ዘመቻ በቁጥጥር ስር ከዋሉት ልኡላንና ባለሃብቶች ወደ አንድ መቶ ቢሊየን ዶላር ለማስመለስ የተንቀሳቀሰው የሳውዳረቢያ መንግስት ከዕቅዱ በላይ ገንዘብ ማስመለሱም ታውቋል።

ለምርመራ ከተጠሩ 381 ሰዎች በአሁኑ ወቅት ሼህ መሀመድ አላሙዲንን ጨምሮ 56ቱ በሪትዝ ካርልተን ሆቴል በእስር ላይ እንደሚገኙ የሳውዲ ባለስልጣናት ተናግረዋል።

በሳምንቱ መጨረሻ የመካከለኛው ምስራቅ ቁጥር አንድ ሀብታም ልኡል አልዋልድ ቢን ታላል በድርድር ገንዘብ ከፍለው ሲወጡ ትላንት ደግሞ ሳላህ ከማል የተባሉ ባለሃብት በድርድር መለቀቃቸውም ተመልክቷል።

የሟቹ የሳውዲ መሪ የንጉስ አብዱላህ ልጅ ልኡል ሚታብ ቢን አብዱላህ አንድ ቢሊየን ዶላር ከፍለው ባለፈው ታህሳስ መፈታታቸው ይታወሳል።

በዚህ የድርድር ሂደት የሳውዲ አረቢያ መንግስት ከጠበቀው 100 ቢሊየን የአሜሪካን ዶላር በላይ 106 ቢሊየን ዶላር ያገኘ ሲሆን ሌሎችንም ለማስከፈል ጥረቱን ቀጥሏል።

የሼህ መሀመድ አላሙዲንን ቤተሰቦች የማሰሩ ርምጃ የቀጠለው በሳቸው ላይ ተጽእኖ ለማድረግ ሳይሆን እንዳልቀረም በዘገባው ተመልክቷል።

በሪትዝ ካርልተን ሆቴል ውስጥ በእስር ላይ ከሚገኙት ባለሃብቶች በሃብት ግንባር ቀደም የሆኑትና በአረቡ አለም በሃብታቸው መጠን በሁለተኛ ደረጃ የተመዘገቡት ሼህ መሀመድ አላሙዲን ከሳውዳረቢያ መንግስት ምን ያህል ገንዘብ እንደተጠየቁ የታወቀ ነገር የለም።

ባለፈው ሳምንት መጨረሻ የተፈቱት የአረቡ አለም ቁጥር አንድ ሃብታም ልኡል አልዋልድ ቢን ታላል 6 ቢሊየን ዶላር እንዲከፍሉ የሳውዳረቢያ መንግስት እንደሚፈልግ መረጃ ወቶ ነበር።

ነገር ግን ምን ያህል ከፍለው ከእስር እንደተለቀቁ የተጠቀሰ ነገር የለም።

በዘመናዊው ሪትዝ ካርልተን ሆቴል እየተጠበቁ የሚገኙት እስረኞች በጥር ወር መጀመሪያ ሃይሪ ወደ ተባለ ወህኒ ቤት እንደተዛወሩ አል አረቢያ አል ጀዲድ የተባለው የአረብኛ ጋዜጣ በዘገባው አቅርቦ ነበር።

ነገር ግን ያቀረበው ዘገባ ስህተት እንደሆነ በቅርቡ ከእስር የተለቀቁት አልዋልድ ቢን ታላል አረጋግጠዋል።

ሆቴሉ መደበኛ አገልግሎቱን በየካቲት ወር አጋማሽ እንደሚጀምር መርሃ ግብር በመያዙ የእነ ሼህ መሀመድ አላሙዲን ማረፊያ እጣ ፋንታ የት እንደሚሆን አልታወቀም።