የርእዮት አለሙ ይግባኝ የህግ እንቆቅልሽ እየታየበት ነው

ታህሳስ  ፳፯(ሃያ ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የፌደራል ይግባኝ ሰሚ ሰበር ችሎት የጋዜጠኛ እና መምህርት ርእዮት አለሙ የይግባኝ ክርክር ትናንት በተናጠል ያደመተ ሲሆን፣ መዝገቡ በአለበት እንደቆመ የቅርብ ቤተሰቦች እና የህግ ባለሙያዎች ለዘጋቢያችን ተናግረዋል።

ስድስት ኪሎ በሚገኘው ሰበር ሰሚ ችሎት የጋዜጠኛው ይግባኝ ከቀረበ ጀምሮ እስካሁን 4 ጊዜ ቀጠሮ የተሰጠው ሲሆን እስካሁንም አቤቱታው መቅረብ እንደሚችል እና እንደማይችል ብይን አላገኘም።
ከተለምዶ የፍርድ ቤቱ አሰራር ውጭ ከዚህ ቀደም በነበረው ቀጠሮ አቃቢ ህግ እና ጠበቃው የቃል ክርክር ያደረጉ ሲሆን ችሎቱ ሲተናነቅም መዝገቡ ለዛሬ ለብኢን የተቀጠረ ቢሆንም ዛሬም እንደገና ጠበቃው የቃል ክርክር ለብቻቸው እንዲያቀርቡ አዲሱ ዳኛ አዘው ጥያቄዎችንም ለጠበቃው አቅርበዋል። ርእዮት አለሙ በድጋሜ ከኤልያስ ክፍሌ ጋር ለምን ተገናኘች፣ ምን ሰራች፣ ምን ተገኘባት የሚሉ ጥያቄዎች ለጠበቃው ቀርበዋል።

ጠበቃ አቶ ሞላ ዘገየም ደንበኛየ ህገ መንግስታዊ መብቷን በመጠቀም በ አንቀጽ 29 መሰረት የሚዲያ ስራ በሪፖርተርነት ሰርታለች፣ አብራቸው የሰራቻቻው ኤልያስ ክፍሌም ሆነ ኢትዮጵያን ሪቪው ድረገጽ በህግ አሸባሪ ተብለው በተወካዮች ምክር ቤት ያልተፈረጁ ናቸው ፣ አቃቢ ህግ በተዘዋዋሪ ለሽብር አላማ ውሎአል የሚለው የህግ ድጋፍ የለውም፣ ይህ በሆነበት ሁኔታ ነው የስር ፍርድ ቤት ፍርድ የሰጠው ብለዋል።

ፍርድ ቤቱም መዝገቡን ይግባኙ ሰበር ሰሚ ችሎት ያስቀርባል ወይስ አያስቀርብም የሚለውን ብይን ለመስጠት ለታህሳስ 30 ቀን 2005 ዓም ከሰአት በሁዋላ የጊዜ ቀጠሮ ሰጥቶ ችሎቱ ተበትኖአል።

ዘጋቢያችን ያነጋገራቸው ምንጮች ” የመሀል ዳኛ አቶ አብድልቃድር ሙሀመድ ፣ ግራ ዳኛ ሱልጣን አባተማም እና በቅርቡ በዚህ ክስ ላይ በመንግስት ሰርገው እንዲገቡ የተሾሙት አቶ መኮንን ችሎት የተሰየሙት የጠበቃውን ክፍተት ተጠቅመው የመንግስትን ውሳኔ እንዲያስፈጽሙ ነው” ብለዋል።

መንግስት ጋዜጠና ርእዮት አለሙን ጨምሮ ሌሎች በሀሰት ወንጀል ተከሰው በእስር ቤት የሚማቅቁትን ጋዜጠኞች እንዲፈታ ከአለማቀፍ የሰብአዊ መብቶች ተከራካሪዎች ተደጋጋሚ ጥያቄ ቢቀርብለትም አሻፈረኝ እንዳለ ነው።