የባለራእይ ወጣቶች ማህበር በደህንነት ሰዎች እየተዋከብን ነው ይላሉ

ታህሳስ  ፳፯(ሃያ ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የማህበሩ ተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበር የሆነው ወጣት አለማየሁ አበበ እና የህዝብ ግንኙነት ሀላፊው ወጣት ብርሀኑ ተክለያሬድ  እንደገለጹት ባለፈው ሳምንት ለኢሳት ቃለምልልስ ከሰጡ በሁዋላ፣ ከአሸባሪዎች ጋር ተገናኝታችሁዋል በሚል በደህንነት ሀይሎች እየተዋከቡ ነው። ከእነርሱ አልፎ ቤተሰቦቻቸውንም ማስፈራራትና ማሸበር መጀመራቸውን ገልጸዋል።

ወጣት ብርሀኑ እንደሚለው በህጋዊነት ተመዝግቦ የሚንቀሳቀሰውን ማህበር የተለያዩ ስሞች እየሰጡ መወንጀልና አመራሮችንም ማዋከብ የሰላማዊ ትግል አስፈላጊነትን ጥያቄ ውስጥ የሚከት ነው

ማህበሩ ባለፈው ሳምንት ሊያካሄድ የነበረውን ጉባኤ ማንነታቸው ካልታወቁ ሀይሎች ለሆቴሎች  በሚተላለፍ ትእዛዝ ምክንያት ሊያካሄዱ አለመቻሉን የገለጸው ወጣት አለማየሁ፣  ይሁን እንጅ አማራጭ በመጥፋቱ በመጪው ሳምንት በአንድነት ፓርቲ አዳራሽ ውስጥ ጉባኤያቸውን ለማካሄድ በመንቀሳቀስ ላይ መሆናቸውን ገልጿል

ጉባኤያችሁን በአንድነት ፓርቲ ማድረጋችሁ የገለልተኝነት ጥያቄ አያስነሳባችሁም በማለት ጥያቄ የቀረበለት ወጣት ብርሀኑ፣ ማህበራቸው ከፖለቲካ ድርጅቶች ጋር በጋራ ተባብሮ የመስራት ፋላጎት እንዳለው መግለጹን ፣ ይህ ማለት ግን የድርጅቶች ጉዳይ አስፈጻሚ ይሆናል ማለት አለመሆኑን ፣ እዚህ ውሳኔ ላይ የተደረሰውም አማራጭ ከማጣት መሆኑን ገልጿል