የሞያሌ ነዋሪዎች የደህንነት ክትትሉ እንዳስመረራቸው ገለጹው

ሰኔ ፱(ዘጠኝ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-2 የአልሸባብ አባላት ናቸው የተባሉ የሶማሊ ተወላጆች መያዛቸውን መንግስት ካስታወቀ በሁዋላ፣ በኢትዮጵያዋ የድንበር ከተማ ሞያሌ ከፍተኛ ጥበቃ እየተካሄ መሆኑንና በዚህም የተነሳ መንግስት በህዝቡ ላይ የሚያደርገው ክትትል እንዳስመረራቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ለኢሳት ገልጸዋል።

መውጫ መግቢያ ማጣታቸውን የሚናገሩት ነዋሪዎች፣ የደህንነት ሃይሎችና ታጣቂዎች ማታ ማታ በግለሰቦች ቤት ሳይቀር እየገቡ ፍተሻ ያካሂዳሉ ብለዋል።

በምሽት ለመውጣት መቸገራቸውን የሚገልጹት ነዋሪዎች፣ የአካባቢውን ታጣቂዎች ከፊት የመከላከያ ሰራዊት አባላት ደግሞ ከሁዋላ ሆነው ቁጥጥር እንደሚያደርጉ፣ በከተማው ሰአት እላፊ ሳይታወጅ፣ ህዝቡ እንደልቡ መንቀሳቀስ እንዳይችል እንደተደረገ አክለዋል።

የአልሸባብ ታጣቂዎች በቅርቡ ወደ ኢትዮጵያ ድንበር ሰርገው በመግባት 33 የኢትዮጵያ ታጣቂዎችን ከገደሉ በሁዋላ በሁለቱ ክልሎች ያለው ጥበቃ ተጠናክሮአል።

የኢትዮጵያ ጦር ካለፉት 2 አመታት ጀምሮ በሶማሊያ ውስጥ እንደሚገኝ ይታወቃል። መንግስት በተደጋጋሚ አልሸባብ እንደተደመሰሰ ቢያውጅም፣ ታጣቂ ሃይሉ ግን አሁንም በኬንያና በሞቃዲሾ ከፍተኛ ጥቃት እየፈጸመ ይገኛል።