የምእራብ ጎጃም ነዋሪዎች በመብራት እጦት መማረራቸውን ገለጹ

መጋቢት ፴ (ሰላሳ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ሰሞኑን በፍኖተ ሰላም እና አጎራባች ወረዳዎች ማለትም በቡሬ ፤ በጃቢ ጠናን ፤ ፈረስ ቤት ፤ ይልማና ዴንሳ፣ ፤ሜጫ ፣ አቸፈር እና ቋሪት የሚኖሩ ነዋሪዎች በፍኖተ ሰላም ከተማ በጃቢ አዳራሽ ከመልካም አስተዳደር ችግሮች ጋር በተያያዘ ከክልሉ መስተዳደር ጋር በተደረገ  ውይይት በመብራት እጦት ለከፍተኛ ችግር መጋለጣቸውን በምሬት ተናግረዋል።

የመብራት ሃይል ሹሞች በሙስና ተዘፍቀዋል ያሉ አንድ ተናጋሪ ፤ ስራቸውን ለመስራት ጉቦ እንደሚጠይቁዋቸውና ለሚመለከታቸው የመንግስት ባለስልጣናት አቤት ሲሉም የሚሰማቸው ማጣታቸውን ገልጸዋል።

የፖሊስ ባልደረባ የሆኑት ዋና ሳጅን አለማየሁ አዲስ በበኩላቸው  መብራት ሃይል መንግስት የማያውቀው በራሱ የሚመራ ድርጅት መሆኑን አስታውሰው፣   ቅሬታችንን ለመንግስት አካላት ስናቀርብ ፖሊሱ ፣ ነዋሪው እንዲሁም ሚኒስትሩ ሳይቀር አሸባሪ ተብሎ እየተፈረጀ ነው ብለዋል።

ዘመኑ አሰፋ የተባሉ የፉነተሰላም ነዋሪ በበኩላቸው በውስጥ ለውስጥ መብራት ችግር ምክንያት የማታ ተማሪዎች በተለይ ሴት ተማሪዎች ለአደጋ እየተጋለጡ መሆኑን ገልጸዋል