የሙስሊም የመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ ችሎት ቢጀምርም የችሎት መጓተት እየተፈታተነው ነው ሲል ድምጻን ይሰማ ገለጸ

ጥቅምት ፬(አራት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ከሳምንታት የችሎት መቋረጥ በሁዋላ ስራ የጀመረው ፍርድ ቤቱ፣ አንድ ምስክር እንካ በአግባቡ ሳያዳምጥ መብራት ሄደ በሚል ምክንያት እንዲቋረጥ መደረጉን ገልጿል።

ሰኞ በነበረው ችሎት አቶ አህመድ ኡመር የተባሉ ምስክር እየተናገሩ ባለበት ጊዜ  ምስክርነታቸው ሳይጠናቀቅ መብራት በመሄዱ ለማክሰኞ ተለዋጭ ቀጠሮ ቢሰጥም ዛሬ ማክሰኞ በተመሳሳይ ሁኔታ ችሎቱ ሳይካሄድ መቅረቱን ድምጻችን ይሰማ ገልጿል፡፡ ለዛሬው ችሎት መቆረጥ የቀረበው

ምክንያት ደግሞ «የኤሌክትሪክ ቆጣሪው ካርድ አልተሞላም» የሚል መሆኑ ተጠቅሷል።

“ለመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላቱ ችሎት መቋረጥ የተለያዩ ምክንያቶች እየተሰጡ ሕዝቡን ለእንግልት መዳረግ እጅግ የተለመደ አሰራር እስከመሆን በደረሰበት የኢትዮጵያ የችሎት አሰራር ከ«ትራንስፖርት አገልግሎት የለም» እስከ «አቃቤ ሕግ አልተመቸውም»፣ ከ«ዳኞች ስልጠና ገብተዋል»

እስከ «የችሎት በር ቁልፍ የለም»፣ ከ«ኤሌክትሪክ ሄደ» እስከ «ፖሊስ እስረኞችን ለማምጣት አልተመቸውም» የሚሉ ምክንያች የተለመዱ አሰራሮች ሆነዋል ብሎአል።

በሌላ ዜና ደግሞ ከ1 አመት ከ6 ወር በላይ በእስር የቆዩ 13 ሙስሊም የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች እንዲፈቱ የከፍተኛው ፍርድ ቤት 14ኛ ወንጀል ችሎት ወስኗል።