የመጪው ምርጫ ተውኔት አስቂኝ ነው ሲል ዘጋቢያችን ገለጸ

በተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወር የኢህአዴግ ካድሬዎች እያደረጉት ያለውን የምርጫ ቅስቀሳና የካርድ እደላ የታዘበው ዘጋቢያችን የምርጫው ሂደት አስቂኝ ሆኗል ብሎአል።
በከምሴ፣ ደብረብርሃን፣ ደብደረማርቆስና ሌሎችም ቦታዎች ካርድ ያለወጡ ሰዎች ኢህአዴግን እንደሚመርጡ ካርድ እየተሰጣቸው ነው። በአንድ ለአምስት፣ በአንድ ለአስር እንዲሁም በቡና ጠጡ መስተንግዶ ዜጎች በቡድን እንዲመርጡ እየተደራጁ ነው። የኢህአዴግ ካድሬዎች በዩኒቨርስቲዎች የቅስቀሳና የማደራጀት ስራ እየሰሩ ነው። ወሎ፣ ድብረብርሃን፣ ጅማና ሃዋሳ ዩኒቨርስቲዎች የኢህአዴግ መናሃሪ በመሆናቸው መምህራን ቅሬታቸውን እየገለጹ ነው።
አዳዲስ የምርጫ ካርዶች ወደ ገጠር እየተላኩ ሲሆን፣ በቅድመ ምርጫ ማሰባሰብ ስም ኢህአዴግን የሚመርጡ አባላት ስም ዝርዝር አስቀድሞ እየተያዘ ነው።
በፓርቲ ተወካዮች ላይ የሚደርሰው አፈናም ተጠናክሮ ቀጥሎአል። በየቦታው የሚሰማው አቤቱታ መልስ አላገኘም የሚለው ዘጋቢያችን፣ ምርጫ ቦርድ ነጻ ፍርድ ከመስጠት ይልቅ ከኢህአዴግ በላይ ሆኖ ለኢህአዴግ ማሸነፍ እየሰራ ነው የሚሉ ቅሬታዎችን መቀበሉን ገልጿል።
በሌላ ዜና ደግሞ ሰማያዊ ፓርቲ ምርጫ ቦርድ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጠይቋል።
ፓርቲው ሚያዝያ 29/2007 ዓ.ም ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በላከው ደብዳቤ በተሻሻለው የምርጫ ህግ 532/1999 ዓ.ም አንቀፅ 58 ቁጥር 1 ላይ የምርጫ ተወዳዳሪዎች ከመዘጋጃ ቤት ፈቃድ ሳይጠይቁ ህዝብ መሰብሰብና ሰላማዊ ሰልፍ መጥራት እንደሚችሉ ቢገለጽም ፣ ፓርቲው ግን ይህንን መብቱን መነፈጉን ገልጿል።
ፓርቲው በመስቀል አደባባይ ግንቦት9 /2007 ዓም ለማድረግ ያሰበውን ህዝባዊ ስብሰባ መስተዳድሩ እውቅና መንፈጉ ተገቢ አለመሆኑን ጠቅሶ፣ ከዚህም አልፎ በፓርቲውና በጸጥታ ሃይሎች መካከል አለመግባባት እንዲፈጠር እያደረገ ነው ሲል ወቅሷል።
የመስተዳድሩ አድልዎ የተሞላበት እርምጃ በኢትዮጵያዊነታችን ላይ ያነጣጠረ አደገኛ ተግባር ነው የሚለው ሰማያዊ፣ ምርጫ ቦርድ እርምጃ እንዲወስድ እንዲሁም መስተዳድሩ ለሚፈጠረው ማንኛውም ችግር ሃላፊነት እንደሚወስድ ገልጿል።