የመንግስት ባለስልጣናት ከቤንሻንጉል ጉሙዝ የተፈናቀሉ አርሶአደሮችን እያነጋገሩ ነው

መጋቢት ፳፮ (ሀያ ስድስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ከአማራ ክልል የተውጣጡ ባለስልጣናት በፍኖተ ሰላም ከተማ ሰፍረው የሚገኙትን የቤንሻንጉል ጉሙዝ አማርኛ ተናጋሪ ተፈናቃዮችን በማነጋገር ላይ መሆናቸውን በሰፍራው የሚገኙ ተፈናቃዮች ገለጡ።
ባለስልጣናቱ ተፈናቃዮቹ የምርጫ ካርዶችን፣ ግብር የከፈሉባቸውን ደረሰኞች፣ የክልሉን መታወቂያ እንዲሁም ሌሎች አባሪ ሰነዶችን አቅርበው እንዲያስመዘግቡ አድርገዋል። ይሁን እንጅ ተፈናቃዮች ወደ መጡበት አካባቢ ስለመመለስ እና አለመመለሳቸው ወይም ሀብትና ንብረታቸው ተመልሶላቸው ወይም ካሳ ተከፍሎአቸው በአካባቢያቸው የእርሻ ቦታ ተሰጥቷቸው እንዲሰፍሩ ስለመደረግና አለመደረጉ ምንም የተባለ ነገር እንደሌለ ተፈናቃዮች ገልጸዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የአሜሪካ ድምጽ ራዲዮ የመኢአድን ስራ አስፈጻሚ አባልና የሰሜን ኢትዮጵያ ተጠሪ የሆኑትን አቶ ተስፋየ ታሪኩን በማነጋገር ፣ ስለተፈናቃዮች እና 59 ሰዎች በመኪና አደጋ መሞታቸውን የተመለከተ ዘገባ ሰርቷል ። በዘገባው አቶ ተስፋየ ሰዎቹ መሞታቸውን ለማረጋጥ አለመቻላቸውን ገልጸዋል
በአሜሪካ ድምጽ የቀረበውን ዘገባ አስመልክቶ የተፈናቃዮችን ጉዳይ ማእከል በመሆን መረጃዎችን በመሰብሰብና በማስተባበር ላይ የሚገኙ አንድ ተፈናቃይ ለኢሳት ሲናገሩ፣ በአቶ ተስፋየ የቀረበው ማስረጃ ለሁለተኛው ጊዜ ስለተገለበጠው መኪና እንጅ ስለመጀመሪያውና 59 ሰዎች ስላለቁበት አይደለም በማለት የተሰጠው አስተያየት ትክክል አለመሆኑን ገልጸዋል። ከእርሳቸው ጋር በፖሊስ ጣቢያ የነበሩ እና ሌሎችም ተፈናቃዮች አስከሬን ለመለየት ተጠርተው መወሰዳቸውን በመጥቀስ አደጋው መከሰቱን በእርግጠኝነት ተናግረዋል።
ኢሳት የተፈናቃዮችን መረጃ በመንተራስ በመኪና አደጋ ስለሞቱት ሰዎች ዘገባ ማቅረቡ የሚታወስ ሲሆን፣ ከመንግስት ወገን ማረጋገጫ ለማግኘት ያደረገው ጥረት ሊሳካለት እንዳልቻለ በተደጋጋሚ ገልጿል።
በአገር ውስጥ የሚገኙም ሆኑ መቀመጫቸውን በውጭ አገራት ያደረጉ ፣ በአገር ውስጥ እንደልብ ተንቀሳቀሰው መዘገብ የሚችሉ ሪፖርተሮች ያሉዋቸው የሚዲያ ተቋማት ፣ ዘጋቢዎቻቸውን ቦታው ድረስ በመላክ እውነቱን ለማጣራት እስካሁን ድረስ ሙከራ ሲያደርጉ አልታዩም። አብዛኞቹ የሚዲያ ተቋማት በሶስተኛ ወገን ከሚሰሙት መረጃ በስተቀር የራሳቸውን ምርመራ ለማካሄድ አለመፈለጋቸው ጉዳዩን እንቆቅልሽ አድርጎታል። ኢቲቪን ጨማሮ የገዢው ፓርቲ ልሳናትም ሆኑ ደጋፊ ሚዲያዎች ለጉዳዩ በቂ ተኩረት ሰጥተው ዘገባ አላቀረቡም። መንግስትም እስካሁን ይፋዊ የሆነ መግለጫ አልሰጠም።
ኢሳት ለጊዜው ዘጋቢዎቹን ወደ አካባቢው በመላክ የ ፎቶግራፍ ማስረጃዎችን ለማቅረብ ባይችልም፣ በቂ ማስረጃዎችን ለማሰባሰብ ከፍተኛ ጥረት እያደረገ መሆኑን ለመግለጽ ይወዳል።