የመንግስት መ/ቤቶች ሐብትና ንብረት በትክክል አለመታወቁ ለብክነትና ለሌብነት እንዲዳረግ ምክንያት ነው ተባለ

መጋቢት ፳፬ (ሀያ አራት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም 

ኢሳት ዜና:-የኢትዮጵያ መንግስት የፌዴራል መ/ቤቶች ሐብትና ንብረት በትክክል አለመታወቁ ለብክነትና ለሌብነት እንዲዳረግ ምክንያት መሆኑን ከፌዴራል የመንግስት ግዥ አስተዳደር የተገኘ ሰነድ ጠቆመ፡፡
የመንግስት የሐብትና ንብረቱ መጠን በትክክል አለመታወቅና ተመዝግቦ አለመያዙ ለጉዳትና ለብክነት በር ከፍቶ
መቆየቱን ሰነዱ ጠቁሞ በመንግስት ንብረት አስተዳደር ያለውን ጉድለት ለመሸፈን ኤጀንሲው ተቋቁሞ ወደስራ ሊገባ
መቻሉን ተመልክቷል፡፡

የመንግስት ንብረት አስተዳደር አዋጅ ቁጥር 649/2001 እና የአፈጻጸም መመሪያ ወጥቶ ስራ ቢውልም በሁሉም
የፌዴራል መ/ቤቶች ከአራት ዓመታት በላይ አዋጁ ተግባራዊ ሊሆን አልቻለም፡፡

የመንግስት መ/ቤቶች የሚገዙዋቸውን ንብረቶች መመዝገብና በማስተዳደር ረገድ ሰፊ ችግሮች እንዳሉባቸው ሰነዱ ጠቅሶ
ይህ ሁኔታ ብክነትና ሌብነት እንዲስፋፋ የራሱን ድርሻ አበርክቷል፡፡

ንብረቶቹ በዘመናዊ መንገድ ተመዝግበው አለመያዝ አላስፈላጊ ክምችት እንዲፈጠር ምክንያት ከመሆኑም ባሻገር ዕቃዎች
በመጋዘን እያሉ ተመሳሳይ ግዥዎች የሚፈጸሙበት ሁኔታ እንዲፈጠር በማድረግ የህዝብ ሐብትና ገንዘብ እንዲባክን
ሲደረግ ቆይቷል፡፡

ኤጀንሲው በፌዴራል በጀት የሚተዳደሩ ተቋማት ዘመናዊና ቀልጣፋ የንብረት አስተዳደር
ስርዓት እንዲዘረጉ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል ተብሏል፡፡

በተለይ የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል በሚፈጸምበት ወቅት በኤግዚቢትነት የሚያዛቸው የተለያ ንብረቶች በፖሊስ አባላት
ጭምር ከረዥም ጊዜ ጀምሮ ስለሚዘረፉ ፍ/ቤቶች እንዲመለስ ቢያዙም እንኳን ለባለቤቶቻቸው የማይመለሱበት አሰራር
ሰፍኖ መቆየቱን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች አስታውሰው ይህ ስርዓት እንዲህ ዓይነቱን አይን ያወጣ ሌብነት
ያስቀራል ተብሎ እንደሚገመት ተናግረዋል፡፡

በተመሳሳይ ሁኔታ በገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን የፌዴራልና የክልል መ/ቤቶች በኮንትሮባንድ የሚያዙ የተለያዩ
ኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች፣ልባሽ ጨርቆች፣ወርቆች፣ልዩ ልዩ የከበሩ ማዕድናት፣የልዩ ልዩ አገር ገንዘቦችና የመሳሰሉት
በተመሳሳይ ሁኔታ ባሉት ቀዳዳዎች መብዛት ምክንያት በየደረጃው ያሉ ሹማምንት ሲሳይ ሆነው የሚቀሩበትን ሁኔታ
መኖሩን በማስታወስ አዲሱ የኤጀንሲው አሰራር ይህንን ለማስቀረት ይሰራል ብሏል፡፡