የህዝቡ የፖለቲካ ተሳትፎ ካልጎለበተ በኢትዮጵያ ጠንካራ ለውጥ አይመጣም ሲሉ የለጋሽ አገራት ቡድን አስታወቀ

 መጋቢት ፲ (አስር) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም 

ኢሳት ዜና:-ተቀማጭነቱ አዲስ አበባ የሆነው የለጋሽ አገራት ቡድን ባወጣው ሪፖርት እንዳመለከተው የኢትዮጵያ መንግስት አገሪቱን ወደ መካከለኛ ገቢ አገር ለመቀየር ማቀዱ በአወንታዊነት የሚመዘገብ ቢሆንም፣ ይህን አላማ እውን ለማድረግ መንግስት የህዝቡን ተሳትፎ ለመጨመር፣ የመልካም አስተዳደር ማሻሻያ ለማድረግ፣ የዲሞክራሲ ተቋማት እንዲገነቡና እንዲጠናከሩ ለማድረግ ጠንካራ እርምጃዎችን መውሰድ አለበት ብሎአል።

ሪፖርቱ አክሎም መንግስት የመቻቻል ባህል እንዲጎለብትን ልዩነቶችን ለማስተናገድ ካልቻለ ፣ የኢትዮጵያ ልማት እውን አይሆንም ብሎአል።

ሪፖርቱ መንግስት በኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የኢኮኖሚ እድገት አሀዝ ለማወቅ የስታትስቲክስ መረጃዎችን ለማጎልበት ጥረት እያደረገ መሆኑን ብንገነዘብም፣ መንግስት መረጃዎች ተአማኒነት ባላቸው ሁኔታ የሚሰበሰቡበትን፣ የተሰበሰቡት መረጃዎች በትክክልና በበቂ ሁኔታ የሚተነተኑበትን መንገድ እንዲቀይስ፣ እስካሁን ድረስ የሚሰራባቸውን የመረጃ መተንተኛ መንገዶች መለስ ብሎ እንዲፈትሽ መክሮአል።

ሪፖርቱ መንግስት ብርካታ የሚሊኒየም የልማት ግቦችን ለማሳካት የጀመረው እንቅስቃሴ ጥሩ ቢሆንም፣ እጅግ በጣም ብዙ ስራዎች እንደሚቀሩ፣ መንግስት እንደሚለው ሁሉንም ነገር አበባ አለመሆኑን ገልጿል።

በሪፖርቱ ማጠቃለያ ላይ መንግስት እስካሁን ላገኛቸው ውጤቶች የልማት ቡድኑ አወንታዊ እውቅና ቢሰጥም፣ ማክሮ ኢኮኖሚውን ለማጠናከር ፣ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት፣ በፌደራል እና በክልል መንግስታት መካከል ያለውን ግንኙነት ለማጠንከር ብዙ ስራዎች እንደሚቀሩ ተመልክቷል።

የለጋሽ አገራት መንግስታት በአፍሪካ ውስጥ ከፍተኛ እርዳታ ከሚሰጡዋቸው አገሮች መካከል ኢትዮጵያ አንዱ ናት። አገራቱ በኢትዮጵያ ያለው የፖለቲካ ተሳትፎ አነስተኛ መሆኑን ቢገልጹም፣ የፖለቲካ ምህዳሩ እንዲሰፋ ስለሚወስዱት እርምጃ ምንም አልጠቀሱም።