ውድ ተመልካቾች ዜና እርማት አለን

ህዳር ፲፱(አስ ዘጠኝ )ቀን ፳፻፮ / ኢሳት ዜና :-ሰሞኑን ጅጅጋን በማስመልከት በተላለፉ ዜናዎች ላይ አንዳንድ ማስተካከያዎች እንድናደርግ የከተማዋ ነዋሪዎች ጠይቀውናል። ኢሳት በብሄር ብሄረሰቦች በአል ምክንያት የጅጅጋ ዩኒቨርስቲ እንደተዘጋ አድርጎ ያስተላለፈው ዜና ስህተት ያለበት ሲሆን የተዘጉት የጅጅጋ ነርሲንግ ማሰልጠኛኮሌጅ እና የጅጅጋ መምህራን ማሰልጠኛ ተቋም እንጅ ዩኒቨርስቲው አለመሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን።

የአቶ መለስ ዜናዊ ሀውልት እንደፈረሰ ተደርጎ በቀረበው ዜናም ላይ ስህተት ያለ ሲሆን፣ ሀውልቱ ከተመረቀበት ጊዜ አንስቶ በህዝብ እንዳይታይ በሸራ ተሸፍኖ እንደሚገኝና እስካሁን እንዳልፈረሰ ለማረጋገጥ ተችሎአል።  ይሁን እንጅ ሀውልቱ እንዲፈርስ ትእዛዝ መሰጠቱን ኢሳት ከትክክለኛ ምንጭ ማረጋገጡን ለመግልጽ ይወዳል።  የክልሉ መንግስት ሀውልቱን አፍርሶ አዲስ እያሰራ ይሁን አይሁን አልታወቀም።  በተፈጠረው የመረጃ ስህተት ኢሳት ከፍተኛ ይቀርታ ይጠይቃል።

ከዚሁ ጋር በተያያዘ ክልሉ ለነዋሪዎች አዲስ መታወቂያ እየሸጠ መሆኑን ለማወቅ ተችሎአል፡፤ ነዋሪዎች መታወቂያ ለማግኘት እስከ 100 ብር እየከፈሉ ነው።

ይህ በንዲህ እንዳለ ባለፈው አርብ አንድ የዩኒቨርስቲ ተማሪ ተግደሎ በመገኘቱ ሶስት ተማሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ምንጮች ገልጸዋል። ተማሪው በምን ምክንያት እንደተገደለ ፖሊስ እስካሁን ይፋ አደረገው መረጃ የለም።