ወጣቱ ፖለቲከኛና ጸሃፊ አብርሃ ደስታ እስር ቤት ውስጥ እንደተደበደበ ለፍርድ ቤት ተናገረ

ነሃሴ ፩(አንድ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ከመቀሌ በሚጽፋው ጽሁፎችና በሚሰጣቸው አስተያየቶች የበርካታ ወጣቶችን ቀልብ የሳበው የመቀሌ ዩኒቨርስቲ መምህር

አብርሃ ደስታ፣ በአሸባሪነት ተከሶ መእከላዊ እስር ቤት ከገባ በሁዋላ ፖሊስ ፍድር ቤት  ያቀረበው ሲሆን፣ አብርሃ በፖሊሶች መደብደቡን፣ እርሱ ያልጻፋቸውን ጽሁፎች

የራሱ ጽሁፎች እንደሆኑ አድርጎ እንዲፈርም መገደዱን፣ በጨለማ ክፍል ውስጥ ብቻውን እንዲቀመጥ መደረጉን እንዲሁም ፖሊሶች ያልሆኑ ሰዎች ምርምራ እንደሚያካሂዱበት

ተናግሯል። በውጭ ከሚጠባበቁ አድናቂዎችና ደጋፊዎች ከፍተኛ አቀባበል የተደረገለት አብርሃም፣ በቤተሰብ እንዳይጎበኝ መደረጉንም ገልጿል።

ፍርድ ቤቱ በዘመድ እንዲጠየቅና አደጋ እንዳይደርስበት ለፖሊስ ትእዛዝ ሰጥቶ ፖሊስ ያቀረበውን የ28 ቀናት የተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ፈቅዷል። በተመሳሳይ መንገድ የሰማያዊ

ፓርቲ የምክር ቤት ምክልት ሰብሳቢ አቶ የሽዋስ አሰፋ፣ አንድንት ፓርቲ ህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ሃብታሙ አያሌውና የድርጅቱ ምክትል የድርጅት ጉዳይ ሃላፊ አቶ ዳንኤል ሽበሺ

ፍርድ ቤት ቀርበው የጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸዋል።

የኢህአዴግ የጸጥታ ሃይሎች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በርካታ ወጣት ጸሃፊዎችንና ፖለቲከኞችን በሽብርተኝነት እየከሰሱ በማሰር ላይ ናቸው። እስረኞቹ የራሳቸው ባልሆነ ጽሁፍ ላይ

እንዲፈርሙ እየተገደዱ መሆናቸውን እየገለጹ ነው።

ድርጊቱ በመንግስት ላይ አለማቀፍ ውግዘት እያስከተለበትም ነው። አምነስቲ ኢንተርናሽናል የመንግስትን ህገወጥ እርምጃ ከመጪው ምርጫ ጋር አያይዞ፣ ጋዜጠኞች፣ ጸሃፊዎችና ፖለቲካኞች

በአስቸኳይ እንዲፈቱ ጠይቋል። ታዋቂ አለማቀፍ የሚዲያ ተቋማትም በተመሳሳይ መንገድ በአንድ ድምጽ እስረኞች እንዲፈቱ ጠይቀዋል።