” ወጣቱ ስርዓቱን እንደማይፈልገው በምርጫ እንቅስቃሴው ወቅት አሳይቷል” አሉ

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲዊ አንድነት መድረክ ቅዳሜ ግንቦት 8 ቀን 2007 ዓ.ም በጃንሜዳ የተጠራውን ህዝባዊ ስብሰባ አስመልክቶ ከኢሳት ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፣ በህዝቡ በኩል በተለይ ወጣቱ መንቀሳቀሱን ይሁን እንጅ ብዙ ቦታዎች ላይ የምርጫ ሜዳው መዘጋቱን ገልጸዋል። ህዝቡ በስሜት ስብሰባዎችን መሳተፉን የገለጹት ዶ/ር መረራ ፣ በምርጫው መቀመጫ ባይገኝ የህዝቡን ትግል ወደ አንድ እርምጃ ለመውሰድ በሚደረገው ሙከራ በብዙ ቦታዎች ላይ ይህን ለማድረግ የቻልን ይመስለኛል ብለዋል። ህዝቡ በተለይ ወጣቱ ” ኢህአዴግን በቃ፣ ኢትዮጵያን የስደተኞች አገር አታድርጋት” የሚሉና ሌሎችንም መልእክቶችን በጋለ ስሜት ማስተላለፉን ዶ/ር መረራ ተናግረዋል።
የፌታችን ቅደሜ በሚካሄደው የመድረክ ህዝባዊ ስብሰባ እስከ 50 ሺ ሰዎች ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል። መድረክ መስቀል አደባባይ ላይ ሰልፉን ለማድረግ ፈቃድ በማጣቱ ጃንሜዳ ለማድረግ ተገዷል። በዚህ ሰብሰባ ላይ ህዝቡ ድምጹን እንዳያሰርቅ መልክት እንደሚተላለፍ ዶ/ር መረራ ተናግረዋል።
በተመሳሳይ ዜና የአዲስ አበባ መስተዳድር በስራ ላይ የሚገኙ 200 መኪኖችን ለአዲስ አበባ ፖሊስ እንዲያስረክብ ታዟል።
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ባለፉት 6 ወራት ልዩ በጀት ተመድቦለት ሲንቀሳቀስ ቢቆይም፣ ሰሞኑን ለፀጥታና ደህንነት አገልግሎት የሚውሉ ከ200 በላይ መኪኖችና ሹፌሮች እንዲዘጋጁለት ለመስተዳድሩ ጥያቄ አቅርቦ ፣ የከተማው አስተዳደርም በስሩ ለሚገኙ ሴክተር መስሪያ ቤቶች ፣ መኪኖቹ ከነነዳጃቸውና የሹፌር አበል ጭምር በመሸፈን ለአዲስ አበባ ፖሊስ እንዲያቀርቡ ሰርኩላር ደብዳቤ ልኳል።
ከፖሊስ ምንጮች የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽነር በየደረጃው ላሉ የፖሊስ የአመራር አካላት ባስተላለፉት ትእዛዝ በምርጫ 97 ወቅት አስጊ የነበሩ ቦታዎች፣ እንዲሁም ልዩ ክትትል የሚፈልጉ አዳዳስ ቦታዎች፣ የመንግስት ባለስልጣናት መኖሪያ አካባቢዎች፣ ከፍተኛ የመንግስት መስሪያ ቤቶች፣ ዩኒቨርስቲዎችና ህዝብ የሚበዛባቸው ተቋማት፣ 4 ኪሎ፣ 6 ኪሎ፣ ፈረንሳይ ሌጋሲዮን እንዲሁም ሌሎች ክ/ከተሞች፣ ወረዳዎችና መንደሮች እንዲለዩና ለተለዩትም አካባቢዎች ልዩ ታጣቂ ሃይል እንዲመደብላቸው እንዲሁም “እግር በእግር በአፋጣኝ መረጃ እንዲላክላቸው ጠይቀዋል።
ከምርጫው ዜና ሳንወጣ ኢህአዴግ በመላ ሃገሪቱ ለምርጫ ማስፈጸሚያ የሚያስፈልገውን ወጪ ከመንግስት ባጀት/ካዝና/ በከፍተኛ መጠን እየተጠቀመ ሲሆን፣ የመንግስት ንብረት የሆኑና ለምርጫ ቅስቃሳ የሚያግዙ ባለድርብ ተግባር የመስክ ተሽከርካሪዎች ፣ ፒክ አፕ መኪና፣ሚኒባስ እና ሞተር ሳይክል፣ ከፍተኛ፣አነስተኛና መለስተኛ የህዝብ አውቶቢሶችን ፣ የመንግስት ሠራተኛውንና ህዝቡን በኢህአዴግ የለሙ መሰረተ ልማቶችን ለማስጎብኘት በሚል ለማጓጓዝ ተግባር እየዋሉ ነው። በመንግስት ወጪ የምርጫ ቅስቀሳ መልዕክት ያዘሉ የህትመት ውጤቶች፣ ኮፍያዎች ፣ባነሮችና ቲሸርቶች ና ፖስተሮች እንዲዘጋጁና ለኢህአዴግ ደጋፊ ለሆኑና ላልሆኑ የማህበረሰቡ ክፍል በሰፊው እንዲሰራጩ እየተደረገ ነው፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ የመንግስት ተሽከርካሪ የሆኑ የሠሌዳ ቁጥራቸው ኮድ 4 የሆነውን ወደ ኮድ 2 እና 3 በመቀየር ገዢው ፓርቲ በሰፊው እየተጠቀመባቸው ነው፡፡
ከምርጫው ዘገባ ሳንወጣ በአዲስ አበባ የሰማያዊ ፓርቲ እጩዎች መታሰራቸውን ሰማያዊ ፓርቲ አስታውቋል።
ፓርቲው በፌስቡክ ገጹ ባሰፈረው መረጃ ግንቦት 5/2007 ዓ.ም የሰማያዊ ፓርቲና በወረዳ 19 የፓርቲው ዕጩ የሆኑት አቶ ኑሪ ሙደሲርን የምርጫ ቅስቀሳ ፖስተሮች ሲለጥፉ የነበሩ የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች በፖሊስ ተይዘው ታስረዋል፡፡ በቅስቀሳ ላይ እያሉ የታሰሩት ምስጋናው ዘመነ፣ ምስረ ጣሂር፣ አብዩ ይታየው፣ ጥላሁን ኃ/ሚካኤል፣ መልካሙ አወቀና ተፈራ በውቄ ናቸው፡፡ ምስጋናው ዘመነና ምስረ ጣሂር የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ሲሆኑ ሌሎቹ ደጋፊዎችና ቅስቀሳውን ሲያግዙ የነበሩ መሆናቸውን ፓርቲው ጠቅሷል።
“የሰማያዊ ፓርቲ አባላት የሆኑት ምስጋናው ዘመነ እና ምስረ ጣሂር ከፍተኛ ድብደባ የተፈፀመናቸው ሲሆን በአሁኑ ሰዓት ላፍቶ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ በእስር ላይ ይገኛሉ” ሲል አክሏል።
የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት መሪ የነበሩት አቶ ማሙሸት አማረ ግንቦት5 ረፋዱ ላይ በአዲስ አበባ ፖሊሶች ተይዘው መታሰራቸውን መዘገባችን ይታወሳል።
በትናንት ዘገባችን በጎንደር አቶ አዋጁ አቡሃይ አደመ እና አቶ አዳነ ባብል ታደሰ የተባሉት ሁለት ግለሰቦች በጸጥታ ሃይሎች መታሰራቸውን የዘገብን ቢሆንም ቶ አዳነ ባብል ታደሰ አለመታሰራቸውን ከቤተሰቦቻቸው ለማረጋገጥ የቻልን ሲሆን፣ አቶ አቡሃይ አደማ ግን አሁንም በእስር ላይ መገኘታቸውን አረጋግጠናል። አቶ አዳነ ባብል ታደሰ እንደታሰሩ ተደርጎ የቀረበው ዜና ስህተት በመሆኑ ይቅርታ እንጠይቃለን።
በመላ አገሪቱ የሚታሰሩ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ሲሆን፣ ገዢው ፓርቲ ምርጫውን ተከትሎ ሊፈጠር የሚችለውን የህዝብ አመጽ አስቀድሞ ለማምከን የወሰደው እርምጃ መሆኑን አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ። በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች ከአዋሽ አርባ 3 ኪሎሜትር ርቆ በሚገኝ ገጠራማ ቦታ ላይ ታስረው ይገኛሉ።