ኮከብ አርማ የሌለው ሰንደቅ ዓላማ ተጠቅማችኃል በሚል የእግር ኳስ ደጋፊ ወጣቶች ተደበደቡ

ሰኔ ፲ (አስር) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:- ኢትዮጵያ ትናንት ደቡብ አፍሪካን ማሸነፉዋን ተከትሎ ምሽት ላይ በነቂስ ወደ አደባባይ ወጥተው ድጋፍ ካደረጉት የባህር ዳር ነዋሪዎች መካከል በዛ ያለ ቁጥር ያላቸው ወጣቶች “የኮከብ ዓርማ የሌለውን  ሰንደቅ ዓላማ በመልበሳቸው፣ እንዲሁም  ‹‹ሰማያዊ ፤ሰማያዊ  ደገመው ዋልያዊ››፣ “ኢትዮጵያዊው ለሰንደቅ አላማው ፤ለሰማያዊው ” እያሉ ደስታቸውን በመግለጻቸው፣ ከፌደራል ፖሊሶች ጋር ውዝግብ ውስጥ ገብተው አምሽተዋል።  ፖሊሶች ሰንደቅ ዓላማውን ለመንጠቅ ባደረጉት ሙከራ አንዳንድ ወጣቶችን ደብድበዋል።

ወጣቶችም “ለባንዴራችን እንሞታለን” እያሉ ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡ አራት ወጣቶች ክፉኛ መደብደባቸውን የገለጸው የባህርዳሩ ወኪላችን፣ ‹‹ ፌደራል የፓርቲ ቅጥረኛ ገዳይ ነው፤ ፤የወንድሞቻችን ደም ፈሶ አይቀርም” በማለት አስፓልት ላይ ቆመው ሲናገሩ ተደምጠዋል።

በግርግሩ መሀል አንድ ሚኒባስ በመገልበጡ ሁለት ወጣቶች ሲሞቱ 4 ደግሞ መቁሰላቸውን ለማወቅ ተችሎአል።

የባህርዳር ከተማ ፖሊስ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ  የሆኑት ኢንስፔክተር ኢሳ ሁለት ወጣቶች መሞታቸውን ቢያምኑም ከሰንደቃላማ ጋር በተያያዘ ከፖሊስ ጋር ተፈጠረ የተባለውን ግጭት ግን አስተባብለዋል።