ኮማንድ ፖስት ተቋቋመ

(ኢሳት ዲሲ– ነሃሴ 4 /2010)በሶማሌ ክልል ያለውን የጸጥታ ሁኔታ ለመቆጣጠር ወታደራዊ ዕዝ ወይንም ኮማንድ ፖስት ተቋቋመ።

ከመከላከያ ሃይል ፣ከፌደራል ፖሊስ እና ከሶማሌ ክልል ልዩ ሃይል የተውጣጣው  ኮማንድ ፖስት በደቡብ ምስራቅ ዕዝ ዋና አዛዥ ሜጀር ጄኔራል በላይ ስዩም እንደሚመራም ታውቋል።

የተቋቋመው ኮማንድ ፖስት  በዛሬው እለት  በክልሉ ጸጥታ ጉዳይ ላይ መወያየቱም ተገልጿል።

የሶማሌ ክልል ፖሊስ ኮሚሽነር እና ሌሎች የፀጥታ ሃይል አዛዦች በተገኙበት በጅጅጋ ከተማ  በተደረገው ውይይት የፌደራልና የክልሉ የፀጥታ ሃይሎች ለክልሉ  ሰላም በትብብር እና በቅንጅት ለመስራት መስማማታቸውን መንግስታዊ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።

ሁሉም የጸጥታ አካላት በመከላከያ ሰራዊቱ ሥር ደቡብ ምስራቅ ዕዝ ዋና አዛዥ ሜጀር ጄኔራል በላይ ስዩም እንደሚመሩም ታውቋል።

በሶማሌ ክልል ባለፈው ሳምንት በተፈጠረው ግጭት የብዙ ሰዎች ሕይወት ሲጠፋ ፣አብያተ ክርስቲናት መቃጠላቸው ንብረት መወደሙም ይታወቃል።

የተደራጁ ታጣቂዎች የሚፈጽሙትን ጥቃት ለመከላከል የሶማሌ ብሄረሰብ  ተወላጆች ጥቃቱን  በመከላከል እና ንብረቶች እንዳይቃጠሉ ለማድረግ መሞከራቸውንም መረዳት ተችሏል።