ከ300 በላይ መኪኖች በጉሙሩክ ተይዘው ለ 2 አመታት ያለስራ መቀመጣቸው ተዘገበ

ግንቦት ፲ (አስር) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-አዲስ አድማስ እንደዘገበው   አስጐብኚ ድርጅቶች፣ የገቢዎችና የጉምሩክ ባለስልጣን ሃላፊዎች አቤቱታችንን ለመስማትም ሆነ እኛን ለማነጋገር ፍቃደኛ ባለመሆናቸው እንግልት ደርሶብናል ሲሉ ባካሄዱት ስብሰባ ገልጸዋል። በመቶ የሚቆጠሩ ድርጅቶች በአባልነት የያዘው የአስጐብኚዎች ማህበር ትናንት በጠራው አስቸኳይ ስብሰባ፣ የፀረ ሙስና ኮሚሽን እንቅስቃሴን እንደሚደግፍ በመግለፅ፣ የኛ አቤቱታና መረጃ ለኮሚሽኑ ጠቃሚ ግብአት ይሆናል ብሏል፡፡

የማህበሩ አባላት የሆኑ አስጐብኚ ድርጅቶች ከባለስልጣኑ መስሪያ ቤት ሃላፊዎች ከባድ ተጽእኖና እንግልት እንደደረሰባቸው ማህበሩ ገልፆ፤ ፀረ ሙስና ኮሚሽን የነሱን መረጃ የሚቀበል ዴስክ እንዲያቋቁም ጠይቀዋል፡፡

አስጐብኚ ድርጅቶች የቱሪዝም ስራቸውን ለማሳደግ ከውጭ ያስመጧቸው ከ300 በላይ መኪኖች ለሁለት አመታት ያለምንም ምክንያት ያለስራ በጉምሩክ ግቢ ውስጥ መቆማቸውን የማህበሩ አባላት ገልፀው፤ ሃላፊዎች ዘንድ ብንሄድም መፍትሔ አላገኘንም፣ የሚያንገላቱና የሚያንጓጥጡ ሃላፊዎች በርካታ በደሎችን ፈጽመውብናል ያሉት የማህበሩ አባላት፣ ይህንን በግልጽ የሚያሳዩ ማስረጃዎቻችን የፀረሙስና ኮሚሽን እንደሚቀበለን ተስፋ እናደርጋለን በማለት አክለዋል።