ከ 30 በላይ አረጋውያን ያለምንም ጥያቄ ታስረው ይገኛሉ ሲሉ ቤተሰቦቻቸው አስታወቁ

ሰኔ ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በኦሮምያ ክልል በጎሬ ወረዳ በንግድ ስራ ይተዳደሩ የነበሩ ከ30 በላይ አረጋውያን ካለፉት 8 ወራት ጀምሮ በእስር ላይ እንደሚገኙ ቤተሰቦቻቸው ለኢሳት ገልጸው፣  የወረዳው ፖሊስ አዛዥ ኮማንደር እውነቱ በቀለ አረጋውያኑ መታሰራቸውን አምነዋል።

አብዛኞቹ እስረኞች እድሜያቸው በ65 እስከ 80 መካከል ሲሆን፣ ብዙዎች እስሩን መቋቋም አቅቷቸው ለተለያዩ በሽታዎችና የመንፈስ ጭንቀት ተዳርገዋል።

አረጋውያኑ በ2001 ዓም የከተማውን መንገድ ለመስራት በሚል ምክንያት መንግስት ቤታቸውን ሲያፈርስባቸው ተገቢ ያልሆነ ክፍያ ተቀብላችሁዋል በሚል ምክንያት ነው የታሰሩት።

ኮማንደር እውነቱ ምርመራው ተጠናቆ ለፍርድ ቤት  መላኩን ገልጸው፣ ፍርድቤቱ ጉዳዩን ለምን እንዳዘገየው ባላውቅም የመጨረሻ ውሳኔ ሊሰጣቸው ይችላል ብለዋል።