ከነገ በስቲያ በኒውዮርክ ታላቅ ሰልፍ ይደረጋል

ሐምሌ ፲ (አስር) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በነ አቶ አንዷለም አራጌ መዝገብ በተከሰሱ ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች ላይ በቅርቡ የተላለፈውን ፍርደ-ገምድል ውሳኔ  እና የዚያኑ ዕለት  ወደ አወሊያ በመግባት በሙስሊም ወገኖች ላይ ታጣቂዎች የፈጸሙትን ጭፍጨፋ በመቃወም ከነገ በስቲያ በኒው ዮርክ ታላቅ ሰልፍ እንደሚደረግ ታወቀ።

የሰልፉ አስተባባቲዎች እንደገለጹት ፤እንደ ፈረንጆቹ አቆጣጠር ጁላይ 19 ቀን ከ 12 ፒ.ኤም እስከ 2 ፒ.ኤም  በኒው ዮርክ   የኢትዮጵያ ኤምባሲ ፅህፈት ቤት ፊት ለፊት በሚደረገው በዚህ ታላቅ የተቃውሞ ሰልፍ ላይ ኢትዮጵያውያን በመገኘት፤ በሀሰት ክስ ለተፈረደባቸው ጋዜጠኞችና የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች፤እንዲሁም መብታቸውን በመጠየቃቸው ሳቢያ ለተጨፈጨፉት ሙስሊም ወገኖቻቸው አጋርነታቸውን  ይገልጻሉ።

የአቶ መለስ ፍርድ ቤት የሀሰት የሽብርተኝነት ክስ በተመሰረተባቸው የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና ጋዜጠኞች ላይ ከ 8 ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ የሚደርስ እስራት በፈረደበት በዚያው ዕለት ምሽት፤ የሰደቃ እና የ አንድነት ፕሮግራም ለማዘጋጀት  በአወሊያ ተሰብስበው ወደነበሩ ሙስሊሞች ታጣቂዎችን በማሰማራት  ጥቃት መፈጸሙ ይታወሳል።

በጋዜጠኞችና በተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮቹ ላይ የተላለፈው ፍርድ፤ ዓለማቀፍ የሰብዓዊና የጋዜጠኞች መብት ተንከባካቢ ድርጅቶችን ጨምሮ በአሜሪካ መንግስትና  በአውሮፓ ህብረት ጠንካራ ተቃውሞ ገጥሞታል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide