ከሳውድ አረቢያ የተባረሩ ዜጎች በችግር ላይ መሆናቸው ታወቀ

ታህሳስ ፴ (ሰላሳ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-መንግስት ከ150 ሺ በላይ ተመላሽ ዜጎችን ወደ ተወለዱበት ቀየ መልሶ በመላክ በአነስተኛ እና ጥቃቅን በማደራጀት የስራ እድል እንደሚፈጥር ቢያስታውቅም፣ ኢትዮጵያውያኑ ወደ ቀያቸው ከተመለሱ በሁዋላ ለከፍተኛ ችግር መዳረጋቸው ታውቋል። ሰሜን ሸዋ አካባቢ በርካታ ስደተኞች መመለሳቸውን የገለጹት ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ አንድ ሰው፣ ተመላሾቹ በአነስተኛ እና ጥቃቅን ትደራጃላችሁ በሚል ተስፋ ቢመጡም፣ ቃል የተገባላቸው ነገር ባለመፈጸሙ ለከፍተኛ ችግር ተዳርገዋል። አንዳንድ ሴቶች በሴተኛ አዳሪነት እየተሰማሩ እንዲሆነ የገለጹት ግለሰቡ፣ ሌሎች ደግሞ ከቤተሰቦቻች ጋር ሳይቀር ግጭት ውስጥ እየገቡ መሆኑን ተናግረዋል።

ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ የሚባለው ታዋቂው ጋዜጣ ባወጣው ሪፖርት ተመላሾቹ ህይወትን ለመላመድ ቀላል እንደማይሆንባቸው የተለያዩ ሰዎችን አነጋግሮ ዘግቧል። በተመላሽ ስደተኞች ምክንያት መንግስትና የተመላሽ ቤተሰቦች ያገኙት የነበረውን ድጋፍ እንደሚያጡም ጋዜጣው ዘግቧል።