ከሜቴክ በቅርቡ ከተገዙት 500 አውቶብሶች 200 የሚሆኑት ከጥቅም ውጭ መሆናቸው ተገለጸ

   (ኢሳት ዲሲ–ሰኔ 5/2010) የአዲስ አበባ አስተዳደር ከሜቴክ በቅርቡ ከገዛቸው 500 አውቶብሶች 200 የሚሆኑት ከጥቅም ውጭ መሆናቸው ተገለጸ።

የከተማው አስተዳደር በሕወሃት የጦር ጄነራሎች ሲመራ የነበረውን ሜቴክን በድርጊቱ ያወገዘ ቢሆንም ፣ የ 3.5 ቢሊዮን ብር ተጨማሪ ሥምምነት ማድረጉ ተዘግቧል።

አዲስ ፎርቹን የከተማው አስተዳደር  አንድ ባለስልጣንን ጠቅሶ እንደዘገበው ከሜቲክ ለአዲስ አበባ ከተማ አንበሳ አውቶብስ ድርጅት የተገዙት አውቶብሶች የጥራት ችግር ያለባቸው ፣ሲበላሹም መለዋወጫ የማይገኝባቸው ናቸው።

እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2013 ከሜቴክ ከተገዙት 500አውቶብሶች ውስጥ መቶ ዘጠና አንዱ 5 ዓመት ሳይሞላቸው  ከሥራ ውጭ ሆነዋል።ሥራ ላይ  የሚገኙት 216 ብቻ እንደሆኑም ታውቋል። ጋራዥ ወስጥ በጥገና  ላይ ከሚገኙት 97 አውቶብሶች ውስጥ 86ቱ የሜቴክ ሥሪት አውቶብሶች እንደሆኑም ተዘግቧል።የሜቴክ አውቶብሶች የከተማውን አስተዳደርም ሆነ የአንበሳ አውቶብስ ድርጀትን ለኪሳራ ቢዳርጉትም ተጨማሪ ሥምምነት መደረጉ አነጋጋሪ ሆኗል። ተጨማሪ አውቶብስ  ለመግዛት የአዲሰ አበባ አስተዳደር ከሜቴክ ጋር የተፈራራመው ውል የ3.4 ቢሊዮን ብር እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል።

ሜቴክ በቅርቡ በፓርላማ ውስጥ ከፍተኛ ትችት እንደደርሰበት ሲታወስ፣በ9 ወራት ሪፖርት የ 9 ቢሊዮን ብር ብክነት ማስመዝገቡም ተመልክቷል፣በፓርላማው የሜቲክ ጥንካሬ ተደርጎ ምስክርነት የተሰጠበት ጉዳይ በህዳሴው ግድብ ላይ  ያለው ተሳትፎ እና ለአዲስ አበባ አስተዳደር የሚያቀርበውን አውቶብስ የተመለከተ ነበር፣ሳምንት ባልሞላ ግዜ ወስጥ ለከተማው አስተዳደር የሚያቀርበው አውቶብስ ችግር ያለበት መሆኑ መጋለጡ የፓርላማ አባላቱ የተሟላ  መረጃ እንደሌላቸው አመልካች ሆኗል።