ከሃሮማያ ዩኒቨርስቲ የወጡ ተማሪዎች ህዝብ እንዲደርስላቸው ጠየቁ

ሚያዚያ ፳፰ (ሃያ ስምንት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ተቃውሞ ተከትሎ  በሀረር መካነሰላም እና በድሬዳዋ መድሃኒአለም ቤተክርስቲያን ተጠልለው የሚገኙ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎች ችግራቸው መፍትሄ ያገኝ ዘንድ ተማጽነዋል።

ከ200 በላይ ተማሪዎች በድሬዳዋ መድሃኒአለም ቤተክርስቲያን ፣ ከ200 በላይ ተማሪዎች ደግሞ በመካነሰላም ቤተክርስቲያን ተጠልለለው የሚገኙ ሲሆን፣ ምንም መረጃ የሌላቸው ተማሪዎች ደግሞ በባዶ ሜዳ እየተንከራተቱ በመለመን ላይ መሆናቸው ታውቋል።

አንዳንድ ተማሪዎች ወደ ቤታቸው ለመሄድ ወይም ወደ ዩኒቨርስቲው ለመመለስ አለመቻላቸውን ገልጽዋል

ምንም እንኳ የዩኒቨርስቲው አስተዳደር ሁኔታው በመረጋጋቱ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዲመለሱ ቢጠይቅም፣ ተማሪዎች በዩኒቨርስቲው አስተዳዳሪዎች ላይ ያላቸው አመኔታ በመቀነሱ ቶሎ ወደ ግቢ  ለመመለስ ፍላጎት አላሳዩም።

አንድ ስሙ እንዳይገለጽ የፈለገ ተማሪ እንደተናገረው በሃሮማያ ዩኒቨርስቲ የደረሰውን የቦንብ ፍንዳታ የግቢው ባለስልጣናት ሆን ብለው ሳያቀነባብሩት አልቀረም። ተማሪው እንደሚለው ፍንዳታው ከመካሄዱ ከሶስት ቀናት በፊት ” ፍንዳታ ይኖራል” የሚል ወሬ ይናፈስ ነበር።

በተመሳሳይ ዜናም ዛሬ በድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ መጠነኛ ግጭት ተከስቶ የነበረ ሲሆን፣ ይህንን ተከትሎ የተወሰኑ ተማሪዎች መታሰራቸው ታውቋል።  

ይህ በእንዲህ እንዳለ የኦህዴድ ከፍተኛ ባለስልጣናት በአምቦ ህዝቡን እያወያዩ ነው። አብዛኞቹ ባለስልጣናት ወደ ተለያዩ አካባቢዎች በመሰማራት ህዝቡን ለማረጋጋት ጥረት እያደረጉ መሆኑም ታውቋል።