እነ እስክንድር ነጋ በዛሬው ዕለት ፍ/ቤት ቀርበው ያለምንም ውጤት ተመለሱ

ህዳር ፲፬ (አስራ አራት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ታዋቂው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና የአንድነት ፓርቲ ም/ሊቀመንበር ወጣቱ ፖለቲከኛ አቶ አንዱዓለም አራጌን ጨምሮ በአሸባሪነት የተከሰሱ ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች በዛሬው ዕለት ፍ/ቤት ቀርበዋል፣ ያለምንም ውጤትም ወደ እስር ቤት ተመልሰዋል።

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ፣ አቶ አንዱዓለም አራጌ ፣ አቶ ናትናኤል መኮንን እንዲሁም አቶ ክንፈ ሚካኤል ደበበ እና ሌሎች በአሸባሪነት ተከሰው እስራት የተፈረደባቸው ኢትዮጵያውያን በዛሬው ዕለት ፍ/ቤት የቀረቡት የፍ/ቤቱን ውሰኔ ተቃውመው ለጠቅላይ ፍ/ቤት ባቀረቡት ይግባኝ ነው።

ከፍተኛ ፍ/ቤት በወጣቱ ፖለቲከኛ አንዱዓለም አራጌ ላይ የእድሜ ልክ እስራት ሲወስን ፣ በጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ላይ የ18 ዓመት እስራት ፣ እንዲሁም በሌሎች ላይ በየደረጃው የእስራት ውሳኔ መስተላለፉ ይታወሳል።

በዛሬው ዕለት ጠቅላይ ፍ/ቤት ለይግባኝ የቀረቡት እነ እስክንድር ነጋ ፍ/በቱ መዝገቡን ለመመርመር በቂ ግዜ ያስፈልገኛል በማለቱ በቀጠሮ ወደ እስር ቤት ተመልሰዋል ፣ ለታህሳስ 10/2005 ቀጠሮ መሰጠቱንም ለማወቅ ተችሎዋል።