ኢትዮጴያዊት የቤት ሰራተኛ በባርነት  ለ 15 ዐመታት መገዛቱዋ ከፍተኛ ትኩረት ከመሳቡም በላይ ጥብቅ የሆነው የቤት ሰራተኞች ህግ መሻሻል እንዳለበት ያመላከተ እንደሆነ ተገለጸ።

ግንቦት ፳፯(ሃያ ሰባት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ሳንዲፕ ሲን ግሪዋል እንደዘገበው፤ ኢትዮጰያዊቱ ሰብለ አበበ ተሰማ  በባህሬይን በቤት ሰራተኝነት  ለ 15 ዓመታት ብታገለግልም፤  የተከፈላት ደመወዝ ከ 18 ወራት ያነሰ መሆኑ  ትናንት የስደተኛ ሰራተኞች ተካላካይ ማህበር  በአድሊያ  በሰጠው ጋሴጣዊ መግለጫ ተወስቱዋል።

በምህጻረ-ቃል “ ኤም.ደብሊው፣ ፒ ኤስ”  የተሰኘው ይህ የስደተኞች ተንከባካቢ ድርጅት እንዳለው፤ ሰብለ በመጀመሪያ ባህሬን የገባችው  እ.አ.አ በ 1999 ዓመተ ምህረት የ 20 ዓመት ልጅ ሳለች እንደነበር በማስታወስ፤ ያኔ በስፖንሰሩዋ ቃል የተገባላት የደመወዝ መጠን በወር 40 ዶላር እንደነበር አመልክቱዋል።

ቃል የተገባላት ደመወዝም በ አሰሪዋ ሊከፈላት ስላልቻለ ስራ በጀመረች በጥቂት ወራት ውስጥ ካሰሪዋ ቤት መጥፋቱዋን የገለጸው ተቋሙ፤ ይሁንና በፖሊስ በመያዙዋ የመጥፋት ሙከራዋ ከሽፎ እንደገና ወደ አሰሪዋ እንድትመለስ መደረጉዋን ገልጹዋል።

.ቤተሰቦቹዋም እርሱዋ ወደ ባህሬን ከሄደች በሁዋላ ከሰፖንሰሩዋ ምንም ዓይነት ገንዘብ ደርሶዋቸው የማያውቁ ከመሆናቸውም በላይ፤ አግብታ በሰላም እየኖረች ሳይሆን አይቀርም ብለው እስከማሰብ መድረሳቸው ተገልጾአል። “

ሀቁ የተጋለጠው የሰብለ ጉዋደኛ የሆነችው እና በኩዋታር የምትኖረው ሰሚራ ባለፈው ወር በባህሬን ጉብኝት ስታደርግ ሰብለ ጋር በመገናኘታቸው እና የምትሰራበትን አስከፊ ሁኔታ በመመልከቱዋ ነው።.

የጉዋደኛዋን  ሁኔታ የተመለከተችው ሰሚራ ወዲያውኑ ጉዳዩን  ለስደተኛ ሰራተኞች ተንከባካቢ ድርጅት ያሳወቀች ሲሆን፤ ድርጅቱም በወንጀል ምርመራ ጀነራል ዳሬክቶሬት -ለህገ ወጥ የሰዎች ዝውውር  ዩኒት  ሪፖርት  አድርጓል።

ይህንኑ ተከትሎ የወንጀል ምርመራው ቢሮ ባልደረቦች  ሰብለን ከምትሰራበት ቤት ወደ ጽህፈት ቤታቸው በማምጣት  ስላለችበት ሁኔታ ለሰዓታት አነጋግረዋታል።

ሰብለ በዙሁ ቃለ ምልልስ በቀድሞ አስሪዋ የደረሰባትን በደል ለድርጅቱ ሪፖርት ለማድረግ እየፈለገች ብአሰሪዋ በመከላከያ ሰራዊቱ ውስጥ ባለው ሀላፊነት በመፍራት ሳትናገር መቆየቱዋን ገልጻለች።

“የህይወቴ መጨረሻ እንዲህ መሆኑን ባሰብኩ ጊዜም ጩኺ ጩኺ ይለኛል”ብላለች-ሰብለ።

የድርጅቱ ጄነራል ሴክሬታሪ ቤቨርሊ ሀማደህ  ለጂ.ዲ.ኤን እንደገለጹት  የሰብለ ቤተሰቦች  ላለፉት 15 ዓመታት ስራ 7 ሺ ዶላር መቀበል ሲኖርባቸው እነሱ የተቀበሉት 600 ዶላር ብቻ ነው።

በአሁኑ ጊዜ ጉዳዩን እየተከታተልን እና  ሰብለ ሊከፈላት የሚገባውን ገንዘብ ታገኝ ዘንድ  ግፊት እያደረግን ነው ብለዋል- ሚስተር ሀማደህ። “