መንግስት አንድ የአልሸባብ ልኡክን መያዙን አስታወቀ

ግንቦት ፳፯(ሃያ ሰባት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- አልሸባብ በኢትዮጵያ ላይ ጥቃት ሊፈጽም ይችላል በሚል ምእራባዊያን አገራት ማስጠንቀቂያ ማውጣታቸውን ተከትሎ፣ ምንም ይፋዊ መግለጫ ሳይሰጥ የቆየው መንግስት፣ ዘግይቶ አንድ የአልሸባብ የጥቃት አቀነባባሪ የሆነ ግለሰብ መያዙን አስታውቋል። መንግስት የግለሰቡን ማንነት ይፋ አላዳረገም።

ከዚሁ ጋር ተያይዞ መንግስት 70 የሚደርሱ የአልሸባብ ወታደሮችን መግደሉን አስታውቋል። ከሶማሊያ የሚወጡ ዘገባዎች በበኩላቸው በአልሸባብና በኢትዮጵያ ወታደሮች መካከል በተደረገው ከፍተኛ ጦርነት ከሁለቱም ወገኖች ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሰራዊት መገደሉን ያመለክታሉ።

የመንግስት ጦር ከአልሸባብ ጋር የተዋጋው አልሸባብ 33 የኢትዮጵያ ወታደሮችን በድንገተኛ ጥቃት ከገደለ ከሳምንት በሁዋላ ነው።