ኢቦኒ የተባለው መጽሄት ተዘጋ

መጋቢት ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ላለፉት 6 አመታት በህትመት ላይ የነበረው ኢቦኒ መጽሄት የተዘጋው ከመንግስት ከፍተኛ የሆነ የግብር እዳ ከተጣለበት በሁዋላ ነው። ጋዜጠኛ በትረ ያቆብ የመጽሄቱን ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ተሰማ ደሳለኝን ጠቅሶ እንደዘገበው የመጽሄቱ አዘጋጆች ሙሉውን ግብር ቀርቶ ግማሹንም ለመክፈል ባለመቻላቸው መጽሄቱን ለመዝጋት ተገደዋል። ድርጅቱ ከወረቀት እና ከሌሎች የህትመት ወጪዎች ጋር በተያያዘ ለከፍተኛ የገንዘብ ችግር ተዳርጎ በሚገኝበት ሰአት የግብር እዳው መምጣቱን ዘገባው አመልክቷል።

ኢቦኒ በመዝናኛ ጋዜጣነት ስራውን ቢጀምርም ካለፉት 2 አመታት ጀምሮ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ጉዳዮችንም መዘገብ ጀምሮ ነበር። ጋዜጠኛው ፖለቲካዊ ይዘት ያላቸውን ጽሁፎች ማተም ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ በደህንነት ሃይሎች እይታ ውስጥ ገብቶ ቆይቷል። የመጽሄቱ የቀድሞው ዋና አዘጋጅ ብስራት ወልደ ሚካኤል በ4 የደህንነት ሰራተኞች ታፍኖ ተወስዶ መደብደቡም በዘገባው ተጠቅሷል።

በወረቀትና በሌሎችም የማተሚያ ወጪዎች የተነሳ እየተንገዳገደ የሚገኘው የተወሰነው የግሉ ፕሬስ ፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ከፍተኛ የሆነ ግብር እየተጣለበት እንዲሽመደመድ እየተደረገ ነው።

አለማቀፍ የሰብአዊ መብት ድርጅቶች ኢትዮጵያ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት የማይከበርባት አገር ሲሉ ይፈርጁዋታል። ከጋዜጠኝነት ስራቸው ጋር በተያያዘ ለእስራት ከተዳረጉት መካከል እስክንድር ነጋ፣ ርእዮት አለሙ፣ ውብሽት ታየና የሱፍ ጌታቸው ይገኙበታል።

በለዘብተኝነተቻው ወይም በኢህአዴግ ደጋፊነታቸው ሳይቀር የሚታወቁት ጋዜጦች ከማተሚያ ቤት ችግር ጋር በተያያዘ በእለቱ አይወጡም።