አንድ የናይጀሪያ ተጫዋች በኢትዮጵያ ደጋፊዎች መመታቱ ተዘገበ

ጥቅምት (አራት)ቀን ፳፻፮ / ኢሳት ዜና :-ቢቢሲ ባወጣው ዘገባ እንደገለጸው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በናይጀሪያ ቡድን መሸነፉ ያበሳጫቸው  ደጋፊዎች የናይጀሪያን ቡድን አሳፍሮ ሲጓዝ በነበረው አውቶቡስ ላይ ድንጋይ በመወርወር አንድ ተጫዋች አቁስለዋል።

ኖሳ ኢግቦር የተባለው ተጫዋች መዳፉ አካባቢ መመታቱን የዘገበው ቢቢሲ፣ የናይጀሪያ ቡድን ባለስልጣናት ክስተቱን ለአለማቀፉ እግር ኳስ ፌደሬሽን ማሳወቃቸውንም ገልጿል።

ድርጊቱን ተከትሎ ምናልባትም ፊፋ በኢትዮጵያ ላይ ቅጣት ሊጥል ይችላል።

በሌላ ዜና ደግሞ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ምርጫ ውስጥ የመንግስት ተጽእኖ ከፍተኛ እንደነበር የሚያሳዩ መረጃዎች ወጥተዋል።

የአማራን ክልል የወከሉት አቶ ተካ አሰፋ በአሁኑ ስዓት የሜድሮክ ኩባንያ እና የሺህ አሊ አላ ሙዲን የህግ ጠበቃ የነበሩ በአማራ ክልል ለፕሬዝዳንትንት ተወክለው የታጩ ሲሆን ምርጫው በሚካሄድበት ስዓት ከደረሳቸው የስልክ ጥሪ በኃላ ከውድድሩ ራሳቸውን አግልለው ምክንያታቸውን በሌላ ጊዜ እንደሚገልጹ ተናግረዋል።

የአቶ ተካ ወደ ውድድር መግባት ከታወቀበት ጀምሮ ካላቸው ከፍተኛ ድጋፍ የተነሳ ውድድሩን እንደሚመሩት እና ምርጫውን እንደሚያሸንፉ ሁሉም ድምዳሜ ላይ ደርሶ ነበር፡፡ አቶ ተካ ላለፉት ስድስት አመታት ፌድሬሺኑን በስራ አስፈፃሚነት በመሩበት ጊዜ  ከተረከቡበት 218 ብር የካዝና ገንዘብ ፣ ለአዲሱ ስራ አመራር 26 ሚልየን ብር በላይ በጥሬ ገንዘብ አስረክበዋል፡፡

ለሉሲዎች እና ለዋያዎች በአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ስዓት አምስት አምስት ሚልየን ብር በድምሩ 10 ሚልየን ብር ሺልማት ቡድኑ እንዲያገኝ በማድረግ ትልቅ ሚናም እንደተጫዎቱ ታውቋል፡፡ ላለፉት ስድስት አመታት ፊድሬሺኑን በስራ አስፈፃሚነት በመሩበት ጊዜ ለኪሳቸው አበል እና ማንኛውንም የትራንስፖርት ወጭ ከኪሳቸው እንደሚሸፍኑ የተገለፀው የአቶ ተካ አሰፋ በድንገት ራሳቸውን ከፊድሬሺን ፕሬዝዳንትነት ምርጫ ማግለል የተቋጠረው ውል በግል በግልጽ ያልተፋታው ውሳኔ በክልሉ በኩል ቅሪታ ፈጥሩዋል፡፡

አቶ ተካ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ እንባ እየተናነቃቸው በቤተሰብ ችግር ነው እራሴን ያገለልኩት ሲሉ ተናግረዋል፡፡

ከቤተሰባቸው ጋር ተያይዞ የተፈጠረው ችግር ይፋ ያላደረጉ ሲሆን፣  ጊዜ ይፍታው ሲሉ መተዋቸው ይታወቃል፡፡

የፊፋ ታዛቢዎች ምርጫው ፍትሃዊ እና ዲሞክራሲያዊ ነው ሲሉ ቢገልጹም ምሐል ላይ የተፈጠረ የተሰወረ አንድ ችግር እንደነበር ለሐገር ውስጥ ጋዜጠኛች ተናግረዋል፡፡

መንግስት  ፌደሬሺኑን መምራት  ያለበት የደቡብ ተወላጅ ነው የሚል አቋም ይዞ እንደነበር ታውቋል።  ይህንን ሴራ ለማክሸፍ ክለቦች ባደረጉት ትንቅንቅ የታሰቡት የደቡብ ተወካይ ሳይሆን ያልታሰቡት የሐረሬ ክልል ተወካይ ምርጫውን አሸንፈዋል።