አንበሳ አውቶቡስ ድርጅት ለመስተዳድሩ ተመለሰ

(ኢሳት ዲሲ–ነሐሴ 28/2010) አንበሳ አውቶቡስ ድርጅት ለአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ተመለሰ።

ድርጅቱ በምርጫ 97 ቅንጅት የአዲስ አበባ ምክር ቤትን ሙሉ በሙሉ ሲያሸንፍ ወደ ፌደራል ከተዘዋወሩ ተቋማት አንዱ ነበር።

በምርጫ 97 የአዲስ አበባ ምክር ቤት በቅንጅት ሙሉ በሙሉ መያዙን ተከትሎ በርካታ የአገልግሎት፣የፋይናንስና የጸጥታ ተቋማት ከከተማው መስተዳድር ወደ ፌደራል መንግስት እንዲዘዋወሩ ተደርጓል።

ስራውን የለቀቀው የፌደራሉ ፓርላማና የሚኒስትሮች ምክር ቤት በመጨረሻ ደቂቃ አዲስ አበባ በቅንጅት አስተዳደር ስር ስትወድቅ የፈሰስ፣የፖለቲካ፣የአስተዳደርና ከፌደራል መንግስቱ ጋር ወደ ፌደራል ከተዘዋወሩት መካከል የአዲስ አበባ መንገድ ትራንስፖርት፣ውልና ማስረጃ፣የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽንና የከተማ አውቶቡስ ድርጅት ይገኙበታል።

ከዚህ በተጨማሪም በአዲስ አበባ አስተዳደር ስር የነበሩ አትራፊ፣ አምራች ድርጅቶችንና ከፍተኛ የገቢ ምንጮች ወደ ፌደራል መንግስት እንዲዘዋወሩ ተደርጎ ነበር።

ይህ የፓርላማውና አስፈጻሚው ውሳኔ በከተማው ሕዝብና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ከፍተኛ ተቃውሞሲቀርብበት ቆይቷል።

ርምጃው የአዲስ አበባ አስተዳደርን ሆን ተብሎ ለማዳከም በሚል በተለያዩ ጊዜያቶች ሕዝቡ ተቃውሞውን ሲያስተጋባ ነበር።

ይህን ተከትሎም በምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ የሚመራው አዲሱ የከተማው ካቢኔ የአንበሳ አውቶቡስ ድርጅት ወደ አዲስ አበባ ከተማ እንዲመለስ ውሳኔ አስተላልፏል።

የአንበሳ ከተማ አውቶቡስ ድርጅት ተጠሪነትም በከተማው ቻርተር መሰረት ለከተማው ዋና ስራ አስኪያጅ እንዲሆን አድርጓል።

የአንበሳ ከተማ አውቶቡስ በፌደራል ስር በቆየበት ሰአት ከፍተኛ ምዝበራ የተካሄደበት መሆኑ በዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት በተደጋጋሚ ሪፖርት የቀረበበት መሆኑ የሚታወስ ነው።