አብዱል ፋታህ አል ሲሲ በከፍተኛ ድምጽ ማሸነፋቸው ተሰማ

ግንቦት ፳፩(ሃያ አንድ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የቀድሞው የግብጽ ወታደራዊ አዛዥ ጄኔራል አብዱል ፈታህ አል ሲሲ 93 በመቶ የሆነ ድምጽ በማግኘት ማሸነፋቸውን የምርጫ ቆጠራ ውጤቶች አመልክተዋል።

ድምጽ ይሰጣል ተብሎ ከተጠበቀው ህዝብ መካከል 46 በመቶ የሚሆነው ብቻ ድምጽ መስጠቱ አል ሲሲ ከገመቱት በታች መሆኑን ቢቢሲ ዘግቧል።

አል ሲሲ የቀድሞውን ፕሬዚዳንት ሙሀመድ ሙርሲን ከስልጣን በማውረዱ በኩል ከፍተኛ ስልጣን እንደነበራቸው ይታወቃል። የሙርሲ ደጋፊዎች ባስነሱት ተቃውሞ ከ1 ሺ 400 በላይ ሰዎች ሲገደሉ፣ 16 ሺ የሚሆኑ ደግሞ ታስረዋል።

ግብጻውያን የሆስኒ ሙባረክን መንግስት ካስወገዱበት ጊዜ ጀምሮ ሰላም እርቋቸው ቆይቷል። ከአብዮቱ በፊት የተካሄደው 2ኛ ምርጫ ለግብጽ አስተማማኝ ሰላም ያመጣላ ተብሎ በብዙዎች ዘንድ ተስፋ አልተጣለበትም።

በመጨረሻም

ውድ ተመልካቾቻችን ሁለት እርማቶች አሉን

በትናንት ዜና ላይ የቀድሞው የአማራ ክልል የወጣቶች ፕሬዚዳንት እና የግንቦት7 ህዝባዊ ሃይል የአመራር አባል የሆነው ዘመነ ካሴ በሽብረተኝነት መከሰሱን በተመለከተ በቀረበው ዘገባ ላይ ዘመነ ካሴ የተከሰሰው በሌለበት መሆኑን ባለመግለጻችን በዚህ መልኩ እንዲታረም እንዲሁም በአዲስ አበባ ከሚፈርሱ ቤቶች ጋር በተያያዘ የኢትዮጵያ መንግስት ከአለማቀፍ ኦሎምፒክ ቃል የተገባለት 2 ሚሊዮን ብር ሳይሆን 200 ሚሊዮን ብር መሆኑን በአክብሮት ለመግለጽ እንወዳለን።