አሜሪካ እና ሩሲያ በዩክሬን ጉዳይ የተራራቀ አቋም መያዛቸውን ፑቲን ተናገሩ

የካቲት ፳፰ (ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የሩሲያው መሪ ቭላድሜር ፑቲን ከአሜሪካው አቻቸው ባራክ ኦባማ ጋር ለ2 ሰአታት ከተወያዩ በሁዋላ ሁለቱ አገሮች በዩክሬን ላይ ያላቸው አቋም የተራራቀ መሆኑን ገልጸዋል።

አሜሪካ፣  ሩሲያ የአለምን ህግ መጣሱዋን በመግለጽ ከዩክሬን ግዛት እንደትወጣና ወደ ድርድር ጠረጴዛ እንድትመለስ ስትሻ፣ ሩሲያ በበኩሉዋ በዩክሬን የሚኖሩ ዜጎቼን ከጥቃት የመከላከል መብት አለኝ በማለት ህግ አለመጣሱዋን ትናገራለች።

ክሪሚያ የምትባለው የዩክሬን ግዛት ፓርላማ ከሩሲያ ጋር ለመቀላቀል ውሳኔ ማሳለፉ፣ ችግሩን የበለጠ አወሳስቦታል። የአውሮፓ መንግስታት በሩሲያ ላይ ማእቀብ ለመጣል መከፋፈላቸውም እየተነገረ ነው። ሩሲያ ማእቀቡ ሁሉንም ወገኖች ይጎዳል በማለት እያስጠነቀቀች ነው።