ነጻ የኢትዮጵያ ሰራዊት ንቅናቄ የኢትዮጵያ ህዝብ በሃገር ውስጥ እና በውጭ አገር በሚያደርገውን ትግል አጋር መሆኑን አስታወቀ።

6 August 2012 [ESAT]  የኢትዮጵያ ህዝቦች በአገር ውስጥና በውጭ ሃገር በመደራጀት እየታገሉ መሆናቸውን ተገንዝቤያለው ያለው ነጻ የኢትዮጵያ ሰራዊት ንቅናቄ ከዚህ የህዝብ አብራክ የወጣ የመከላከያ ሰራዊትም በህቡዕ ተደራጅቶ የትግል አካል ለመሆን መዘጋጀቱን በመግለጫው አስታውቋል::   የንቅናቄው ቃል አቀባይ ሻምበል ኤፍሬም ተካ ከኢሳት ሬድዮ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ እንደገለጹት የኢትዮጵያ መከላከያ የፖሊስና የደህንነት ኃይል በህቡዕ ሲደራጅ መቆየቱን አመልክተው ለትግል ለተዘጋጀው የኢትዮጵያ ህዝብ መከታ ሆኖ ከጎኑ ለመቆም ዝግጅቱን አጠናቋል ብሏል። በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ በጎሰኝነት የሚራመድ መንግስት የሚያደርሰው መከራና ግፍ ሰራዊቱ ውስጥ በከፋ መልኩ ይደርስብናል ያለው ይህ መግለጫ ከዚህ በኋላ ለጥቂት የህውሃት ባለስልጣናት መጠቀሚያ አንሆንም ይልቁንም ከህዝባችን እንሰለፋለን ብሏል።  የነጻው የኢትዮጵያ ሰራዊት ንቅናቄ ዛሬ ላይ ለመድረስ ሰፊ ስራ ሰርቷል ያሉት ቃል አቀባይ ኤፍሬም ተካ የሰራዊት አመራር በአብላጫው ከአንድ ጎሳ መሆናቸው መጠነኛ ፈተና ሊሆን እንደሚችልም በማመን አንድነታችንን አጠናክረን መከራውን ማለፍ የሚያስችለንን ስትራቴጂ ቀይሰናል ብለዋል::