ታዋቂው አትሌት ሻለቃ ኃይሌ ገብረስላሴ የኢትዮጵያ ፕሬዚዳንት ሆኖ በገዥው ፓርቲ ኢህአዴግ ሊመረጥ እንደሚችል ተጠቆመ

ሐምሌ ፭( አምት )ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና :-ሻለቃ ኃይሌ ፕሬዚዳንት የመሆን ፍላጎት እንዳለው ለዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን መግለጹን ተከትሎ ኢህአዴግ መራሹ
ራዲዮ ፋና ባልተለመደ መልክ ዜናውን ደጋግሞ እንዳራገበው አንድ የፖለቲካ ተንታኝ ጠቅሰው ፣ ሀይሌ የሰጠውም መግለጫ ሆነ የሬዲዮ  ፋና ዘገባ በድንገት የሆነ ሳይሆን ታቅዶበት የተደረገእንደሚሆን ግምታቸውን አስቀምጠል፡፡

በአሁኑ ወቅት በስልጣን ላይ የሚገኙት መቶ አለቃ ግርማ ወ/ጊዮርጊስ ሁለተኛውን የሥልጣን ዘመናቸውን ከአንድ ወር በኋላ
የሚያጠናቅቁ ሲሆን በመስከረም ወር 2006 መጨረሻ አዲስ ፕሬዚዳንት በፓርላማው አብላጫ ወንበር ያለው ገዥው
ፓርቲ ኢህአዴግ ዕጩ አቅርቦ ያስመርጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

እስከቅርብ ጊዜ ድረስ በፓርላማ የግል ተመራጭ የሆኑት የጥርስ ሐኪም ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ ፕሬዚዳንት ሊሆኑ ይችላሉ የሚል ሰፊ ግምት ተሰጥቷቸው የቆዩ ሲሆን እሳቸውም ለኢህአዴግ ያላቸውን ታማኝነት በየአጋጣሚው ሲያሳዩና ሲገልጹ መክረማቸው የሚታወስ ነው፡፡

ኃይሌ ሰሞኑን ፕሬዚዳንት እንደሚሆን መግለጫ የሰጠው ምናልባት ከኢህአዴግ ታጭቶና እሱም ዕጩነቱን ተቀብሎ ሊሆን
እንደሚችልና ይህም ወሬውን አስቀድሞ ሕዝብ ውስጥ በማስገባት የልብ ትርታውን የማዳመጥ ጉዳይ ሊሆን እንደሚችል ጠንካራ
ግምታቸውን አስቀምጠዋል፡፡