በ ደቡብ አፍሪካ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ደማቅ የተቃውሞ ሰልፍ አደረጉ

ግንቦት ፪ (ሁለት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ኢትዮጵያውያኑ ሰልፉን ያደረጉት ገዥው የኢህአዴግ መንግስት ኢትዮጵያ ውስጥ እየፈጸማቸው ያሉትን ኢፍትሀዊ እና ህገ ወጥ ድርጊቶች በመቃወም ነው።

በርካታ  ኢትዮጵያውያን በተሳተፉበት በዚህ ሰልፍ፤ ገዥው ፓርቲ ዜጎችን በዘር እየመረጠ ከመኖሪያ ይዞታቸው ከማፈናቀል ተግባሩ እንዲገታ፣ አላግባብ የታሰሩት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ፣ ጋዜጠኞች፣የሙስሊም መሪዎችና ሌሎች የህሊና እስረኞች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ! መንግስት በሀይማኖት ተቋማት ጣልቃ መግባቱን እንዲያቆም፣በዋልድባ ገዳምና በሎሎች ታሪካዊ ቅርሶች ላይ እየፈፀመ ካለው የማፍረስ ድርጊት እንዲገታ ጥያቄዎች ቀርበዋል።

መነሻውን ጆሀንስበርግ አድርጎ የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት መቀመጫ በሆነው ፕሪቶሪያ ባቀናው በዚህ ደማቅ ሰልፍ ላይ እስከ 1000 ኪሎ ሜትር ርቀት ካላቸው ቦታዎች የመጡ ይገኙበታል።

ሰልፉን በተመለከተ የደቡብ አፍሪካ ተባበሪ ዘጋቢያችን ዝናሽ ሀብታሙ በሰልፉ ላይ የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶችን የሚወክሉና እና ከሁሉም ብሄር ብሄረሰቦች የተሰባሰቡ ኢትዮጵያውያን መገኘታቸውን ገልጻለች።

የደቡብ አፍሪካው መሪ ጃኮብ ዙማ  እና የተበባሩት መንግስታት ድርጅት ተወካዮች የኢትዮጵያውያንን ጥያቄ ተቀብለዋል።