በጎንደር እስር ቤት ለሁለተኛ ጊዜ በእስረኞች ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደረሰ

ኀዳር ፳፫ (ሃያ ሦስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በጎንደር ከተማ ከቀኑ 4፡30 ጀምሮ እስሰ 7፡00 ሰዓት የተክስ ልውውጥ ተካሂዷል፡፡ ሰሞኑን በተፈጠረው የአስር ቤቱ ቃጠሎ ህይወታቸው ያለፉት እስረኞች ቤተሰቦች ‹‹ እስር ቤቱ እስረኞችን ሊያስተምርና ወደ መልካም ህይወት ሊለውጥ እንጅ የራሱን ምክንያት እየፈጠረ ሊገድል አይችልም፡፡የሞቱ ልጆቻችንና ወንድሞቻችንን አስከሬን ስጡን ፡፡›› በሚል ጭቅጭቅ በተፈጠረ አለመግባባት መሳሪያ ከታጠቁት የሟች ቤተሰቦች ጋር የተኩስ ልውውጥ ተካሂዷል ሲል ዘጋቢያችን ገልጿል።
በተኩስ ልውውጡ ቁጥራቸው ያልታወቀ እስረኞች በመቁሰላቸው ወደ ሆስፒታል መወሰዳቸውን ታውቋል፡፡የተጎጂ ቤተሰቦች በለቅሶና ዋይታ ሆስፒታል አካባቢ ተሰባስበው ታይተዋል።
ሌሎች የአይን እማኞች በበኩላቸው እስረኞቹበግቢው ውስጥ በነበረ የጭድ ክምር ላይ እሳት በመለኮስ ተቃውሞአቸውን መግለጻቸውንና አጋጣሚውን ተጠቅመውም ከእስር ቤት ማምለጣቸውን ተናግረዋል።
ጠያቂዎች ምግብ ይዘው ሲሄዱ፣ ቅዳሜ ቀን ካልሆነ ዛሬ መስጠት አትችሉም በመባላቸውና ጠያቂዎችም የሞቱ ቤተሰቦች ካሉ ንገሩን በማለት ጥያቄ በማቅረባቸው እስረኞቹ ከውስጥ አመጽ እንዲያስነሱ እንደገፋፋቸው አንዳንድ በቦታው የነበሩ የአይን እማኞች ተነጋርዋል ።
ስለደረሰው ጉዳት ለማወቅ ለከተማው ፖሊስ ጣቢያ ስልክ ብንደውልም፣ መረጃውን ለማጠናከር የሄዱት ፖሊሶች ባለመመለሳቸው መረጃ ለመስጠት አንችልም ብለዋል በሌላ በኩል ደግሞ ከ9 ያላነሱ የፖለቲካ እስረኞች ተቃውሞውን ሆን ብለው አስነስተዋል በሚል ተወስደው መረሸናቸውን የፖሊስ ምንጮች ገልጸዋል። አሸናፊ በተባለ ደህንነት ሌሊት ተወስደው የተረሸኑት እስረኞች በፖለቲካ ምክንያት የታሰሩ ከአርማጭሆና ወልቃይት አካባቢ የመጡ ሰዎች ናቸው።
ከሶስት ቀናት በፊት በደረሰው ቃጠሎ ከ100 በላይ እስረኞች ማምለጣቸው ታውቋል፡፡ 14 እሰረኞች ካመለጡ በኋላ ተይዘዋል፡፡ሁለቱ ቤተክርስቲያን ውስጥ ሲያዙ ፣አንዱ በመኪና ተሳፍሮ ሲሔድ ማክሰኝት ላይ መያዙን ምንጮች ገልጸዋል።
ቃጠሎው በተፈጠረ ጊዜ ህብረተሰቡ በፖሊስ የተከበቡትን እስረኞች እንዲያመልጡ ከፍተኛ እገዛ ሲያደርግ እንደ ነበር ጉዳዩ የሚመለከታቸው የመንግስት ባለስልጣናት በቁጪት ሲናገሩ ተሰምተዋል፡፡ ህዝቡ ውስጥ ሩጠው ከገቡ በኋላ እንዳይተኮስባቸው በመከለል በርካታ እሰረኞች እንዲያመልጡ አድርገዋል በማለት ባለስልጣናቱ በህዝቡ ላይ ቅሬታቸውን ሲገልጹ ተሰምቷል።