በጉጂ ዞን የሚካሄደው ተቃውሞ ቀጥሎአል

በጉጂ ዞን የሚካሄደው ተቃውሞ ቀጥሎአል
(ኢሳት ዜና ሚያዝያ 23 ቀን 2010 ዓ/ም) ሜድሮክ ኢትዮጵያ በሻኪሶ አካባቢ ላለፉት 20 አመታት ሲያወጣ የነበረው የወርቅ ማእድን በዜጎች ጤና እና በተፈጥሮ ላይ ያስከተለውን ውድመት በመጥቀስ፣ ኩባንያው ተጨማሪ ፈቃድ እንዳይሰጠው የጠየቁ የአካባቢው ነዋሪዎች ተቃውሞአቸውን ወደ አደባባይ በመውጣት እየገለጹ ነው። ትናንት የተጀመረው ተቃውሞ ዛሬም በተለያዩ የዞኑ ከተሞች የተካሄደ ሲሆን፣ ተቃውሞው ከዚህ ቀደም ይታይ እንደነበረው መንገዶችን በመዝጋት ተግባራዊ እየተደረገ ነው። ዛሬ በሻኪሶ ዙሪያ ከተሞች በተካሄደው የመንገድ መዝጋት እና የአደባባይ ተቃውሞ እስካሁን የአንድ ሰው ህይወት ማለፉ ታውቋል። ሌሎች በርካታ ዜጎች ደግሞ ቆስለው አዶላ ሆስፒታል ገብተዋል። በመቶዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች መታሰራቸውንም የአካባቢው ነዋሪዎች ለኢሳት ገልጸዋል።
ከክብረመንግስት ወደ ሻኪሶ፣ ከክብረ መንግስት ወደ ቦረና የሚወስደው መንገድ የተዘጋ ሲሆን፣ የአጋዚ ወታደሮች መንገዱን ለማስከፈት ሙከራ ሲያደርጉ ውለዋል።
የአካባቢው ነዋሪዎች ከሚድሮክ በተጨማሪ የለያዩ የውጭ ኩባንያዎችም ማእድኑን እየጫኑ እየወሰዱት መሆኑን ይናገራሉ። ደኖች መጨፍጨፋቸውን የአካባቢው ህዝብ ለበሽታ መደራጉን ነዋሪዎች ይገልጻሉ
የአካባቢው የጤና ባለሙያዎችና ነዋሪዎች ሚድሮክ ኢትዮጵያ ለወርቅ ማውቻ የሚጠቀምበት ሳናይድ የተባለው ኬሚካል ጉዳት እያመጣ እንደሆነ ሲናገሩ ፣ ኩባንያው በበኩሉ የወርቅ ማምረት ስራው የአካባቢውን ተፈጥሮ በሚንከባከብ መልኩ እንደሚካሄድ ይገልጻል።
የማእድን ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ ሚኒስቴር የአካባቢ እና የማህበረሰብ ልማት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሆኑት ወ/ሮ እናት ፋንታ “እስከ መጋቢት 2009 ዓ.ም ባደረግነው ክትትልና ቁጥጥር መሰረት በኬሚካል የደረሰ ጉዳት አላየንም፤ ከማህበረሰቡም ሆነ ከመንግስት አካል የደረሰንም ቅሬታ የለም” በማለት ለቢቢሲ ተናግረዋል።
በ1989 ዓ.ም የለገደንቢን የወርቅ ማእድን ከመንግስት እጅ በ172 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ለ20 ዓመታት በሊዝ የተረከበው ሚድሮክ የኮንትራት ስምምነቱ በዚህ አመት የሚያበቃ ቢሆንም፣ ማእድን ሚኒስቴት ለተጨማሪ 10 አመታት የሚቆይ የፈቃድ እድሳት ማድረጉ ለተቃውሞው መነሻ ሆኗል።