በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ዝርፊያ እየተፈጸመባቸው ነው

በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ዝርፊያ እየተፈጸመባቸው ነው
(ኢሳት ዜና ሚያዝያ 17 ቀን 2010 ዓ/ም) ኢትዮጵያኑ እንዳሉት የአገሪቱ ዜጎች የፖለቲካ ተቃውሟቸውን ለመግለጽ ወደ አደባባይ ከወጡ በሁዋላ የስደተኞችን ንብረቶች በመዝረፍ ከፍተኛ ጉዳት አድርሰዋል።
ኢሳት ያነጋገራቸው ኢትዮጵያውያን እንደገለጹት፣ በዝርፊያው በርካታ ኢትዮጵያውያን ሃብትና ንብረታቸውን አጥተዋል።
በሌላ በኩል ሕጋዊ የመኖሪያ ፈቃድ የሌላቸው 26 ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ሞዛንቢክ ውስጥ ተያዙ
በሕገወጥ መንገድ ሞዛምቢክን አቆራርጠው ወደ ደቡብ አፍሪካ በመጓዝ ላይ የነበሩ ያላቸውን ቁጥራቸው 26 የሚሆኑ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞችን ማኒካ አውራጃ ውስጥ መያዛቸውን የአገሪቱ የፖሊስ ባለስልጣናት አስታወቁ። የአገሪቱ መንግስታዊ ሬዲዮ ጣቢያ ባለስልጣናቱን ጠቅሶ ማክሰኞ እለት እንደዘገበው ስደተኞቹ ይጓጓዙበት የነበረው ተሽከርካሪም ከስደተኞቹ ጋር በፖሊስ በቁጥጥር ስር ውሏል።
በእስር ላይ ያሉት ኢትዮጵያዊያኑ ስደተኞች በሙሉ ወንዶች ሲሆኑ እድሜአቸው ከ19 እስከ 40 ዓመት እንደሚሆናቸው የማኒካ ፖሊስ ጣቢያ ቃል አቀባይ ኮማንደር ኤልሲዲያ ፊሊፔ አስታውቀዋል። ስደተኞቹ ማላዊን አቆራርጠው ባለፈው ዓርብ ወደ ሞዛቢክ የገቡ ሲሆን ምሽት ላይ በቁጥጥር ስር ከመዋላቸው አስቀድሞ በጫካ ውስጥ ለ24 ሰዓታት ተደብቀው ቆይተዋል።
የአካባቢው ነዋሪዎች ባደረጉት ጥቆማ መያዛቸውን ቃል አቀባዩ አክለው ገልጸዋል። ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በተደጋጋሚ ጊዜያት በሕገወጥ መንገድ ወደ ሞዛምቢክ እንደሚገቡና ሕጋዊ ሂደቶችን ተከትሎ ወደ ትውልድ አገራቸው እንደሚመለሱ ኤ.ኤፍ.ፒን ጠቅሶ ጆርናል ዲ ካሜሩን ዘግቧል።