በደቡብ ሱዳን የሚገኙ ኢትዮጵያውያን መንግስት እንዲታደጋቸው እየተማጸኑ ነው

ታህሳስ ፲፰ አስራ ስምንት )ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ዩኒቲ በሚባለው ግዛት ውስጥ የሚገኙ ኢትዮጵያን በጦርነት አጣብቂኝ ውስጥ መገኘታቸውንና ህይወታቸው አደጋ ውስጥ መውደቁን ተናግረዋል።

በግዛቱ ውስጥ በአንድ የመንገድ ስራ ድርጅት ውስጥ ተቀጥረው የሚሰሩ 6 ኢትዮጵያውያን እንደተናገሩት በሁለቱ ተፋላሚ ሀይሎች መካከል የሚደረገውን የተኩስ ልውውጥ ለማምለጥ ያለፉትን ሁለት ቀናት በከባድ ማሽነሪዎች ውስጥ በመደበቅ ለማሳለፍ ተገደዋል። በአካባቢያቸው 2 ኢትዮጵያውያን መገደላቸውንና 3ቱ ደግሞ መቁሰላቸውን ተናግረዋል።

እስካሁን ድረስ ምን ያክል ኢትዮጵያውያን እንደሞቱ ባይታወቅም፣ የአሜሪካ ድምጽ ራዲዮ በአገሪቱ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን በማነጋገር እንደዘገበው የሞቱ ኢትዮጵያውያን ቁጥር እስከ ታህሳስ 17፣ 2006 ዓም ድረስ ቢያንስ 30 ይደርሳል።

ኢሳት ያነጋገራቸው ኢትዮጵያውያን እንደሚሉት መንግስት እስካሁን ድረስ ዜጎቹን ለመሰብሰብ ጥረት እያደረገ አይደለም። ጎረቤት አገሮች ኬንያና ኡጋንዳ ዜጎቻቸውን ሲያስወጡ የኢትዮጵያ መንግስት ምንም አይነት እርምጃ ለመውሰድ አለመፈለጉ ለብዙዎች እንቆቅልሽ ሆኗል። ኢትዮጵያውያን አሁንም መንግስት እንዲደርስላቸው ጥሪ አቅርበዋል

በጆንግሌ ግዛት የተደፈሩ 4 ኢትዮጵያውያን ጁባ ውስጥ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሆስፒታል ውስጥ ህክምና እንዲያገኙ ተድርጓል።x

ይህ በእንዲህ እንዳለ የምስራቅ አፍሪካ መንግስታት በናይሮቢ ኬንያ ያደረጉትን ስብሰባ ተከትሎ የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር በግላቸው ተኩስ እንደሚያቆሙ አስታውቀዋል። አገራቱ የመንግስትን እርምጃ የደገፉ ሲሆን፣ የኬንያው መሪ ኡሁሩ ኬንያታ በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠን መሪ በሀይል ለማውረድ የሚደረገውን እንቅስቃሴ እንደማይደግፉ ገልጸዋል።

የተቃዋሚዎች መሪ የሆኑት ሪክ ማቻርም በተመሳሳይ መንገድ ተኩስ እንዲያቆሙ የምስራቅ አፍሪካ መሪዎች ተማጽኖ አሰምተዋል። መሪዎቹ በሚቀጥሉት 4 ቀናት ፊት ለፊት ተገናኝተው እንዲወያዩ ኢጋድ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል።እስካሁን በተካሄደው የእርስ በርስ ጦርነት ከ1 ሺ በላይ ሰዎች መገደላቸውን አለማቀፍ የመገናኛ ብዙሀን ዘግበዋል;፡