በደሴ ዙሪያ አንድ ህዝብን ያሰቃያል የተባለ ሹም ተገደለ

ግንቦት ፲፪ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ግንቦት6 ቀን 2005 ዓም ከቀኑ ስድስት ሰአት ላይ ሙሀመድ የሱፍ የተባለ የደሴ ከተማ ቀበሌ 12 ነዋሪ የ ቀበሌያቸውን የመሬት አስተዳደር ሹም አቶ አህመድ እንድሪስን በ2 ጥይቶች በመግደል ማምለጡ ታውቋል።

ገዳይ አቶ ሙሀመድ የጦር መሳሪያ ከሌላ ታጣቂ ላይ በመቀማት ነው የቀበሌ ሹሙን ገድለው የተሰወሩት። ሟቹ ባለስልጣን የአካባቢውን አርሶአደሮች መሬት በመቀማት፣ ማዳበሪያ በግድ እንዲወስዱ በማስደረግ እንዲሁም ጉቦ በማስከፈል ከፍተኛ በደል ሲፈጽም እንደነበር ያነጋገርናቸው ሰዎች ገልጸዋል። ህብረተሰቡ ገዳይ በወሰደው እርምጃ ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማው ድርጊቱ ሲፈጽም የነበረ አንድ ግለሰብ ለኢሳት ገልጿል። ገዳይ ከሟች ጋር ምንም አይነት የግል ጸብ ያልነበራቸው ሲሆን ድርጊቱን የፈጸመው የህዝቡን ስቃይ ተመልክቶ መሆኑን እኝሁ ግለሰብ አክለው ተናግረዋል።

በጉዳዩ ዙሪያ የደሴን ፖሊስ ጽህፈት ቤት ባለስልጣናት ለማነጋገር ሙከራ ብናደርግም አልተሳካልንም።