በምዕራብ ጎጃም ሜጫ ወረዳ ሰዎች በግፍ እየታሰሩ ነው

ግንቦት ፲፪ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ፍኖተ ነጻነት እንደዘገበው ሚያዚያ 18 ቀን 2005ዓ.ም. በሜጫ ወረዳ መራዊ ከተማ ከሚገኙ ነዋሪዎች መካከል አቶ አንሙት እና አቶ መንግስት በቀለ የተባሉ ወጣቶች በሌሊት በታጣቂዎች ታፍነው ተወስደዋል።

ግንቦት 3 ቀን 2005ዓ.ም. ከሌሊቱ 9፡00 ሰዓት መኮንን     አድማስ በሚባል የፀጥታ ኃላፊ እና ወ/ሮ አሰለፈ ከበደ በሚባሉ የወረዳው ካቢኔ በመራዊ ከተማ ነዋሪ የሆኑትን ወ/ሮ ሙሉ ሲሳይን በሁለት ተሸከርካሪዎች በሄዱ የፀጥታ ኃይሎች አሽባሪ ነሽ፣ የደበቅሽውን ቦምብ አምጭ በሚል ከፍተኛ ድብደባ ፈጽመውባት ወዳልታወቀ ቦታ እንደወሰዷት ጋዜጣው ዘግቧል።

በመራዊ ከተማ ከግንቦት7 ጋር ግንኙነት አላችሁ የተባሉ ሁለት ወጣቶች ታፍነው መወሰዳቸውን አንድ ግለሰብም እጅ አልሰጠም በማለት መሸፈታቸውን መዘገባችን ይታወሳል።