በውጭ የሚገኘው ሲኖዶስ መንግስት የሚፈጽመውን የማፈናቀል እርምጃ አወገዘ

መጋቢት ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በውጭ የሚገኘው እና በ ብጹእ አቡነ መርቆርዮስ የሚመራው ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የኢሕአዴግ መንግሥት አገራችንን ኢትዮጵያን በጠመንጃ ኃይል ከተቆጣጠረበት ጊዜ አንሥቶ  የኢትዮጵያ አንድነት ከባድ አደጋ ውስጥ ጥሎታል” ብሎአል።

 

 ኢህአዴግ የዘር ማጥፋት ዘመቻውን መልኩን በመቀያየር በቦረናና በአርባ ጉጉ፥ በጋምቤላና በኦጋዴን፥ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ በአፋር፣ በደቡብ ኢትዮጵያ እና በቤኒሻንጉል በሚኖሩት ወገኖቻችን ላይ እየፈጸመ ነው የሚለው መግለጫ፣  “ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህ እየተከናወነ ያለው የዘር ማጥፋት ዘመቻ ጥቂቶች በብዙዎች ላይ ነግሠው እንዲኖሩ ለማድረግ የታቀደና የኢትዮጵያን አንድነት አደጋ ላይ የሚጥል በመሆኑ በመላው ዓለም ያሉ ሕዝቦች ድምጹ ለታፈነበትና በሰቆቃ ላለው ሕዝብ ድምጽ በመሆን በዓለም የተለያዩ መድረኮች ጩኸቱን እንድናደርስለት ጥሪ ታቀርባለች።” ብሎአል።

 

ቅዱስ ሲኖዶሱ”   በኢትዮጵያና በመላው ዓለም የምትገኙ የልዩ ልዩ እምነት ተካታይ ወገኖቻችን በዚህ በታላቁ የሕማማትና የትንሣኤ በዓል ጊዜ ክርስቲያን ወገኖቻችን ከቦታቸው ተፈናቅለው መናንያን መነኮሳት ከገዳማቸው ተሰደው በሰቆቃና በአንባ እየታጠቡ የሚገኙበት ጊዜ  ገዥው ፓርቲ ከግፈኝነቱ እንዲታቀብ፤ ወገኖቻችንን በቋንቋና በዘር መለያየቱን እንዲያቆምና መናኝ መነኮሳትን ማሳደዱን እንዲያቆም በአንድነት እንድትነሱ በእግዚአብሔር ስም ጥሪ እናቀርባለን። ” ብሎአል በመግለጫው።

ሲኖዶሱ በአገር ጠባቂ ስም የተቀመጡ የደህንነትና የሠራዊት አባላት በሙሉ የህዝብ እንጂ የመንግስት አገልጋይ እንዳልሆኑ አውቀው ከህዝብ ጎን እንዲቆሙ፣  ለኢትዮጵያ ሕዘብ መልካም አስተዳደር ለማምጣት በአማራጭነት የሚታገሉ የፖለቲካና የሰብዓዊ መብት ደርጅቶች በሙሉ  ልዩነቶቻቸውን አስወግደው በመመካከርና በአንድነት ኢትዮጵያና ህዝቧን ከጥፋት ለማዳን እንዲደርሱ እንዲሁም  በአሁኑ ጊዜ በተለያየ ምክንያት በቡድን፤ በግል፤ በቤተሰብም ሆነ በድርጅት የተቀያየሙ ወገኖች አንድነታቸው እጅግ የሚያስፈልግበት ወቅት በመሆኑ በዚህ ሕማም ሳምንትይቅር እንዲባባሉ ጠይቋል።