በኬንያ በርካታ ሴቶች ታፍነው ተወሰዱ።

ሰኔ ፰(ስምንት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-አልሸባብ እንደፈጸመው በተጠቀሰው ጥቃት 48 ሰዎች በተገደሉ ማግስት፣ ሌሎች ተጨማሪ 12 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን፣ ከ12 ያላነሱ ሴቶችም በታጣቂዎች ታፍነው መወሰዳቸውን ቢቢሲ ዘግቧል።

ምፔኬቲኒ እየተባለ በሚጠራው የወደብ ከተማ ላይ የደረሰውን ተከታታይ ጥቃት አልሸባብ እንደፈጸመው እየተዘገበ ባለበት ወቅት፣ የአገሪቱ መሪ ኡሁሩ ኬንያታ ፣ ጥቃቱ በራሳቸው ባለስልጣናት የተቀነባበረና ከጎሳ ጋር የተያያዘ መሆኑን በመግለጽ፣ አልሸባብ ፈጸምኩ የሚለውን ጥቃት አስተባብለዋል።

በአካባቢው የሚገኙ የፖሊስ አዛዦች ከሃላፊነት እንዲነሱ ያደረጉት ፕሬዚዳንቱ ለፍርድ እንደሚቀርቡም ተናግረዋል።

አልሸባብ በበኩሉ ኬንያ ጦሩዋን ከሶማሊያ እስካላስወጣች ድረስ ጥቃቱ እንደሚቀጥል ተናግሯል።