በእስር ላይ የሚገኘው እውቁ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ የ2014 የፔን አለማቀፍ ሽልማት አሸናፊ ሆነ

ጥር ፳ (ሃያ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የድርጅቱ ሊቀመንበር የሆኑት ቶማስ ብሩኒጋርድ ” እስክንድር አፋኝ የፕሬስ ህግ ባለበት አገር በድፍረት ለመጻፍ በመቻሉ ሽልማቱ እንደተሰጠው ገልጸው፣ የኢትዮጵያ መንግስት እስክንድርን ጨምሮ በአሸባሪነት ታስረው የሚገኙትን ሰሎሞን ከበደ፣ ውብሸት ታየ፣ ርእዮት አለሙ እና የሱፍ ጌታቸውንም እንዲለቅ ጠይቀዋል።

የፔን አለማቀፍ  ሽልማት ለፕሬስ ነጻነት ለሚታገሉት ጋዜጠኞች በእየአመቱ የሚሰጥ ሽልማት ነው። ከዚህ በፊት ጋዜጠኛ ሲሳይ አጌናም ይህን ሽልማት ማሸነፉ ይታወቃል።

ጋዜጠኛ እስክንድር የ18 አመታት ጽኑ እስራት እንደተፈረደበት ይታወቃል። ካለፉት 2 አመታት ጀምሮ በእስር ላይ የሚገኘው ጋዜጠኛ እስክንድር ለብዙ ወጣቶች የጽናት ምሳሌ መሆኑን በማህበራዊ ሚዲያዎች የሚወጡ አስተያየቶች ያመለክታሉ።