በኢትዮጵያ ከሚሊዮን በላይ በልመና የሚተዳደሩ ሰዎች አሉ ተባለ

ነሃሴ ፴(ሠላሳ)ቀን ፳፻፭ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የሰራተኛ እና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የማህበራዊ ኑሮ ጠንቆች ሲል ባስጠናው እና በዓመቱ መጠናቀቂያ በወርሐ ጳጉሜ ይፋ በሚያደርገው መረጃ እዳመለከተው የልመና ተዳዳሪነት በሐገሪቱ ላይ ጥቁር ጥላውን እያጠላበት ሲሆን ከጊዜ ወደ ጊዜ የቱሪስቶች የደህንነት ስጋት ከመሆን ባለፈ ለዜጎችም መትረፋቸውን ገልጿል።

በመገባደድ ላይ ባለው በ2005 ዓ.ም ብቻ በአማራ ክልል ከሶስት መቶ ሺ ፣ በትግራይ ከሁለት መቶ ሺ በላይ ዜጎች  በየቤተ ክርስቲያኑ እና በየቤተ እምነቱ ተጠልለው ሲለምኑ፤ ደቡብ እና ሐረሬም ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ለማኞች ይገኛሉ። በአዲስ አበባም በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ለማኞች በከተማዋ እንደሚገኙ ይታወቃል።

በኢትዮጵያ አስቸኳይ የምግብ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ከ3 ሚሊዮን በላይ ዜጎች ሲኖሩ  8 ሚሊዮን የሚጠጉት ደግሞ በሴፍትኔት ወይም ምግብ ለስራ ታቅፈዋል።