በኢትዮጵያ ባለፉት 5 ዓመታት ብቻ ከ70 ቢሊዮን ብር በላይ ገንዘብ ወደ ውጭ ተሻግሯል

ግንቦት ፳፯ (ሃያ ሰባት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ግሎባል ፋይናንሻል ኢንተግሪቲ ባወጣው ልዩ ዘገባ በፈረንጆች አቆጣጠር ከ2008 እስከ 2012 ባለው ጊዜ ውስጥ ከኢትዮጵያ በተለያዩ ህገወጥ መንገዶች ከ70 በሊዮን ብር ወይም
ከ3 ቢሊዮን 550 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገንዘብ ወደ ውጭ ወጥቷል።
በ5 ዓመታት ውስጥ ተሰርቆ የወጣው ገንዘብ ወደ አገሪቱ ከገባው የውጭ የቀጥታ ኢንቨስትመንት መጠን ጋር ሲተያይ በ1 ሺ 355 በመቶ ይልቃል። ከአገሪቱ አጠቃላይ አመታዊ ምርት ጋር ሲነጻጸር ደግሞ 11 ነጥብ 2 በመቶ ይሸፍናል።
ተቋሙ በህገወጥ መንገድ የሚወጣው ገንዘብ በአገሪቱ ውስጥ ድህነትን እያባበሰ፣ በዜጎች መካከል ኢፍትሃዊ የሆነ የሃብት ክፍፍል ልዩነት እየፈጠረ እንዲሁም ዝቅተኛ የሆነ የሰዎች ልማት እንዲፈጠር እያደረገ ነው።
ከ82 በላይ አገሮችን ያጠናው ተቋሙ፣ ገንዘብ ወደ ውጭ ከሚሸሽባቸው መንገዶች ማካከል የተጭበረበረ ንግድና ሙስናና ዋነኞቹ ናቸው ብሎአል።
ከድሃ አገሮች በህገወጥ መንገድ የሚወጣውን የበለጸጉት አገሮችና የተባባሩት መንግስታት ድርጅት እንዲያስቆሙ ደርጅቱ ጠይቋል። በሚቀጥለው ወር በአዲስ አበባ በሚደረገው ሶስተኛው የልማት እርዳታ ላይ መንግስታት ትኩረት እንዲያደርጉበት
የተለያዩ የፖሊሲ አማራጮች አቅርበዋል።
ተቋሙ ከዚህ ቀደም በፈረንጆች አቆጣጠር ከ200 -2009 ባሉት አመታት 11 ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ ገንዘብ ወደ ውጭ መውጣቱን ይፋ አድርጎ ነበር።