በኢትዮጵያ ስራ የጀመሩ የውጭ ባለሃብቶች ቁጥር አነስተኛ ነው ተባለ

ሚያዚያ ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በኢትዮጵያ ባለፉት ሶስት ዓመታት ወደ ኢንቨስትመንት ለመግባት ፈቃድ ከወሰዱት የውጭ አገር ባለሃብቶች መካከል ወደሥራ የገቡት ከግማሽ በታች መሆናቸውን ከኢንቨስትመንት ባለስልጣን የተገኘ መረጃ አመልክቷል፡፡

ባለፉት ሶስት ዓመታት 187 ነጥብ 31 ቢሊየን ብር ካፒታል ያላቸው 2ሺህ 164 ያህል የውጭ ባለሃብት ፈቃድ የተሰጣቸው ሲሆን  እስካሁን 50 ቢሊየን ብር  ካፒታል ያስመዘገቡ 770 ባለሃብቶች ማለትም ካፒታላቸው 28 ነጥብ 28 ቢሊየን ብር የሆነ 637 ፕሮጀክቶች ወደማምረት የተሸጋገሩ ሲሆን ፣ ካፒታላቸው 21 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር የሆነ 133 ፕሮጀክቶች ግንባታ ላይ መሆናቸውን ይጠቅሳል፡፡

ፈቃድ ከወሰዱት ውስጥ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው 1 ሺህ 394 ያህሉ በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ መረጃው አይጠቅስም፡፡

ፈቃድ ከወሰዱት የውጭ አገር ባለሃብቶች መካከል የቱርክ 46 ነጥብ 12 ቢሊየን ብር በማስመዝገብ ቀዳሚ ሲሆኑ የሕንድ ፕሮጀክቶች 32 ነጥብ 34 ቢሊየን ብር ፣ የቻይና 9 ነጥብ 82 ቢሊየን ብር  ተከታታዩን ደረጃ ይዘዋል፡፡ ወደማምረት ከተሸጋገሩት ፕሮጀክቶች አንጻር ሲታይ ብዙ ፕሮጀክቶችን የያዙት የቻይና፣ የሱዳን፣ የቱርክ፣ የሕንድ፣ እና የአሜሪካ ኩባንያዎች ናቸው፡፡